የመጋቤ ሐዲስ ኀይለ እግዚእ አሰፋ በ2018 ዓ.ም የአህጉረ ስብከት የሰ/ት/ቤቶች የአሠልጣኞች ሥልጠና መክፈቻ መርሐ ግብር ላይ ያስተላለፉት መልእክት

ብፁዕ አቡነ ማርቆስ በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ ሊቀ ጳጳስ፣

ክቡር መጋቤ ሐዲስ ጸጋ ወልደ ትንሣኤ የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ ዋና ሐላፊ

ዲ/ን ስንታየሁ ምስጋና  የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት  ተቀዳሚ ምክትል ሰብሳቢ

ክቡራን የሰንበት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ አገልጋዮችና የሀገር አቀፍ የሰንበት ትምህርት አንድነት አመራርና  አገልጋዮች

ክቡራን ከየአህጉረ ስብከቱ የመጣችሁ ወድሞቻችንና እኅቶቻችን፣

ከሁሉ አስቀድሞ ልዑል እግዚአብሔር በሰላምና በጤና ጠብቆ፣ በአባታዊ ፍቅሩ ጠርቶ፣ በበረከቱ  ጎብኝቶ፣ በሰላም አምጥቶ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ በሀገር አቀፍ ሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት ከሐምሌ 6  እስከ ሐምሌ 21 ቀን 2018 ዓ.ም በቅድስት ሥላሴ ዩንቨርሲቲ አዳራሽ የሚሰጠውን የመምህራን አሠልጣኞች ሥልጠና በብፁዓን አባቶቻችን ቡራኬ እንደዲከፈት ስለ ፈቀደልን  ለስም አጠራሩ ክብር ምስጋና ይድረሰው እያልኩ  ብፁዓን አባቶቻችን ልጆቻችሁንን ለመባረክና አባታዊ መልእክት ለማስተላለፍ ፣ ወንድሞቻችንም በሀገር አቀፍ ደረጃ በሚሰጠው የሥርዐተ ትምህርት ትግበራ ላይ  ሥልጠናውን ለመከታተል የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችሁን ድምፅ ሰምታችሁ መዋቅራችሁን አክብራችሁ በመምጣታችሁ የተሰማኝን ደስታ በመመሪያችን ስም እየገለጽኩ  ሁላችሁም እንኳን ደኅና መጣችሁ  እያልኩ ትንሽ መልእክት እንዳስተላልፍ ይፈቀድልኝ ዘንድ በአክብሮት እጠይቃለሁ፡፡

“ዘጸምአ ይምጻእ ኀቤየ ወይስተይ ወዘሂ የአምን ብየ አፍላገ ማየ ሕይወት ይውሕዝ እምከርሡ” “የተጠማ ወደ እኔ ይምጣና ይጠጣ፣ በእኔም የሚያምን መጽሐፍ እንደተናገረ የሕይወት ውኃ ወንዝ ከሆዱ ይፈልቃል” (ዮሐ7፡37) ይኸን ቃል የተናገው መድኅነ ዓለም ክርስቶስ ነው፡፡   ቃሉም የተነገራቸው በሥልጠና ላይ ለነበሩ ደቀ መዛሙርት ነው፡፡ ቃሉን ጠጥተው ጽምዐ ነፍሳቸውን እንዲያርቁ፣ ከዓለማዊ ግብር እንዲላቀቁ፣ በሃይማኖትና በምግባር እንዲልቁ  ፣ ጸጋ መንፈስ ቅዱስን አንዲለብሱ፣ ከብሌት እንዲታደሱ፣ በአእምሮ እንዲጎለብሱ ስለጠራቸው “የተጠማ ወደ እኔ ይምጣና ይጠጣ” በማለት የሰውን ልጆች ሁሉ ወደ እርሱ ጠርቷቸዋል፡፡  በመተርጒማን ዘይቤ ደረቅ ሐዲስ በሚል  የትንቢት መጽሐፉ የሚታወቀው ነገረ ክርስቶስን በተመለከተ በምልአትና በስፋት የጻፈው ልዑለ ቃል ኢሳይስም  “እናንተ የተጠማችሁ ሁሉ  ወደ ውኃ ሂዱ”  ሲል ትንቢታዊ ምክሩን ለግሶአል፡፡ ( ትን .ኢሳ 55፡1)

ለሐዋርያነት በመረጠው በክርስቶስ አንደበት “ንዋይ ኅሩይ” “ምርጥ ዕቃ” የተሰኘው ቅዱስ ጳውሎስም “ምድርኒ ለእመ ሰትየት ዝናመ ዘይመጽእ ላዕሌሃ ትወልድ ሣዕረ ሠናየ ሶቤሃ ዘበእንቲኣሁ ሐረስዋ ወትነሥእ በረከተ እምኀበ እግዚአብሔር” “ምድርም በእርስዋ የሚወርደውን  ዝናም ከጠጣች ያን ጊዜ ስለ እርሱ ያረሱላትን መልካም ቡቃያ ታበቅላለች ከእግዚአብሔርም ዘንድ በረከትን ታገኛለች” ብሏል፡፡

የሰው ልጅ ከተፈጠረባቸው አራቱ ባሕርያት መካከል አንዱ ውኃ ነው፡፡  በሥነ ተፈጥሮ ከሰው እስከ እንስሳት፣ ከአራዊት እስከ ዕፀዋት ውኃን ይፈልጋሉ፡፡ ሁሉም የውኃ ጥገኞች ናቸው፡ በተለይ የሰው ልጅ ልብሱን የሚያጥብበት፣ ንጽሕናውን የሚጠብቅበት፣ ምግቡን የሚያዘግጅበት፣  ቢጠማው ጥሙን የሚያርቅበት፣ እንደ ዛሬው መስተዋት በሌለበት ዘመን መልክአ ገጹን የሚመለከትበት አእምሮውን የሚያዝናናበት ውኃ ነው፡፡ ተፈጥሮው ከውኃ ጋር የተሳሰረ ነውና፡፡ የውኃ ጥቅምና አገልግሎት እጅግ  ብዙ ነው፡፡

በልዑለ ቃል ኢሳይያስ አገላለጽ ውኃ፡- የትምህርት፣ የልጅነት፣ የሀብተ ክህነት ምሳሌ ነው፡፡

ልዑለ ቃል ኢሳይያስ  እናንተ የተጠማችሁ ወደ ውኃ ሂዱ ማለቱ እስራኤል ዘሥጋ በፋርስ በባቢሎን ሰባ ዘመን በስደት ከኖሩ በኋላ “ማርና ወተት ወደ ምታፈስሰው ምድረ ከነዓን ተመልሰው የተራቡት በልተው እንደ ሚጠግቡ የተጠሙት ጠጥተው እንደሚረኩ ሲያመለክት  የተጠማችሁ ሁሉ ወደ ውኃ ሂዱ ብሏል፡፡

አስራኤል ዘሥጋ የተራቡና የተጠሙት ከምግበ ሥጋ ብቻ አልነበረም  ምግበ ነፍስ ከሆነው ከቃሉም  ተርበውና ተጠምተው ስለ ነበር በመዓር የተመሰለው  ብሉይ ኪዳን በወተት የተመሰለው ሐዲስ ኪዳን በመጀመሪያ በትንቢት በመቀጠልም በገቢር ወደ ሚተረጐምባት የተስፋ ምድር ተመልሰው ጽምዐ ነፍስ ተወግዶላቸው ክብራቸው ተመልሶላቸው  “ንሥኣ ወብልዓ ለእንታክቲ መጽሐፍ”  “እንካ ይህችን መጽሐፍ ብላት”  “ሲሲተ ልብ ቃላቲሁ ለእግዚአብሔር  የእግዚአብሔር ቃል የአእምሮ (የነፍስ) ምግብ ነው” እንዲል ቃሉን ተመግበው እንደ ውኃም ጠጥተው ረክተው የሚኖሩ መሆናቸውን ያሳያል፡፡  “እኔ ከምሰጠው ውኃ የሚጠጣ ለዘለዓለም አይጠማም ያ እኔ  የምሰጠው ውኃ በውስጡ ለዘለዓለም ሕይወት  የሚፈልቅ የውኃ ምንጭ ይሆንለታል”  እንዳለ ጌታ (ዮሐ 4፡14)፡፡

በክርስቶስ  ትምህርት ውኃ፡- የቅዱስ ወንጌል፣ የመንፈስ ቅዱስ ምሳሌ መሆኑን ያመለክታል፡፡

የሐዋርያው የቅዱስ ጳውሎስ መልእክትን አንድምታ ትርጓሜ ያዘጋጁ መተርጒማን ደግሞ ምድር የሚማር ደቀ መዝሙር (ሠልጣኝ)  ዝናም ቃለ እግዚአብሔር፣ ገበሬው መምህር፣ መሆኑን በአብርሆት ትርጓሜያቸው ያስረዳሉ፡፡  የገበሬው ተግባር ማረስ፣ መዝራት፣ ማረም መንከባከብ ነው፡፡ ገበሬው ይዘራል እንጂ አንዱን ቅንጣት ሰላሳ፣ ሥልሳ፣ መቶ ማድረግ አይችልም አሠልጣኝ መምህርም ተግቶና ነቅቶ ያስተምራል እንጂ በሠልጣኞቹ አእምሮ ቃሉን ጽፎ ሠላሳ ሥልሳ መቶ ማድረግ አይችልም ይህን ማድረግ  የእግዚአብሔር ድርሻ ነውና፡፡

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፡፡

የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የሥራ ሐላፊዎች

ክቡራን ከየአህጉረ ስብከቱ የመጣችሁ አሠልጣኝ መምህራን፡፡

መምህረ ዓለም ቅዱስ ቄርሎስ “ይእዜኒ ደቂቅየ ጽሑቃን ወፃእክሙ ዝየ ወመላእክሙ ቤተ ክርስቲያን እንዘ ጽሙኣን አንትሙ ትትረወዩ ማየ ዘቤተክርስቲያን ወይፍረይ ልብክሙ ፍሬ ሠናየ በከመ ሀብተ ማይ ያበቊል ፍሬሃ ለምድር ዘወትረ ይሠቅይዋ ከማሁ ቃሎሙ ወትምህርቶሙ ለአበው ቅዱሳን  እለ ተምህሩ በኲሉ ጥበብ ወአእምሮ ይበውእ ውስተ አልባበ ሰብእ ለመድኀኒት ይእዜኒ ንዑ ጽሙኣን ወናረውየክሙ ጽምዐክሙ  ነሢአነ እምጳውሎስ ጠቢብ ማየ እስመ ነቅዐ ሕይወት ውእቱ”

ዛሬም ለትምህርት የምትተጉ ልጆቼ ትምህርትን ወዳችሁ ወደ ጉባኤ መጥታችኋል፤ የቤተ ክርስቲያንን ውኃ ትጠጡ  ዘንድ ማለት  የቤተ ክርስቲያን ትምህርት ትማሩ፣ ልቡናችሁም በጎ ፍሬን ያፈራ ዘንድ፤ ቤተ ክርስቲያንንም መልታችኋል፡ የውኃ ለምድር መሰጠት ጥዋት ማታ የሚያጠጧት የምድር ፍሬን እንዲያስገኝ  ፍጹም ጥበብን የተማሩ የሊቃውንት ምክራቸውና ትምህርታቸው ሕይወት ለመሆን በሰው ልቡና ያድራል፤ አሁንም ትምህርትን የምትወድዱ ወደ ጉባኤው ኑ  ከጥበበኛው ጳውሎስ ትምህርት አግኝተን አጠጥተን እናረካችኋለን፤ የጳውሎስ ትምህርት የሕይወት ምንጪ የድኅነት መገኛ ነውና (ተረፈ ቄርሎስ ምዕ 23፡5)፡፡

በመሆኑም ቤተ ክርስቲያናችን ካሏት የትምህርት ተቋማት አንዱ የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ነው፡፡ ይህ መመሪያ ከመንበረ ፓትርያረክ እስከ አጥቢያ ድረስ መዋቅሩ የተጠናከረ ከሀገር አቀፍ ሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት ጋር እየተናበበ የሚሠራ ሥራዎቹንም ከንግግር ባለፈ በተግባር ገልጦ ያሳየ  ታላቅ መምሪያ ነው፡፡ በተለይ ከአንደኛ እስከ ዐሥራ ሁለተኛ ክፍል በተለያዩ ቋንቋዎች በሀገር አቀፍ የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት የታተሙትና  እየታተሙ ያሉት  መጻሕፍት መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት  በፈቀደው በጀት፣ በመምሪያው የበላይ ሐላፊ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ አባታዊ መመሪያና ክትትል፣ በመምሪያው የሥራ ሐላፊዎች ትጋት፣ በሀገር አቀፍ ሰንበት ትምህርት ቤቶች  አንድነት ከፍተኛ ጥረት  የተከናወነ  በመሆኑ መምሪያችን ለሁሉም ምስጋናውን  ያቀርባል፡፡ ጉባኤውንም እንዲያመሰግንልን ይጠይቃል፡፡

በመጨረሻም ከአህጉረ ስብከት የመጣችሁ ሁላችሁም የነገዋ ቅድስት  ቤተ ክርስቲያን ተረካቢ ልጆች እንደ መሆናችሁ መጠን እናታችሁ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ምግበ ነፍሱንና ምግበ ሥጋውን ለእናንተ አዘጋጅታ “ንዑ ብልዑ ኅብስትየ ወስትዩ  ወይንየ ዘቀዳሕኩ ለክሙ ወኅድግዋ ለእበድ ወኅሡ አእምሮ ከመ ትሕየዉ” “ኑ እንጀራዬን ብሉ፤የጠመቅሁላችሁን  የወይን ጠጅም ጠጡ፤ ስንፍናን ትትችሁ በሕይወት ኑሩ” ትላችኋለች (ምሳሌ 9፥5)፡፡  እናንተም የእናታችሁን ምክር ሰምታችሁ በምክሯ ስትኖሩ ደግሞ “ እምዛቲ ትፍሥሕት እንተ ተዐቢ አልብየ ከመ እስማዕ እንዘ በጽድቅ የሐውሩ ደቂቅየ” ልጆቼ በእውነት ሲሄዱ ከመስማት የበለጠ ደስታ የለኝም በማለት የእናትነት ደስታዋን በአደባባይ  ትገልጥላችኋለች፡፡

ስለሆነም በቆይታችም እንደ ንብ በምጥቀስሙት የቃል አበባ  የተግባር ማር ወለላን ሠርታችሁ ስትመለሱ ወድሞቻችሁንና እኅቶቻችሁን እንድተመግቡቸው ረክታችሁ እንድታረኩአቸው የእግዚአብሔር ፈቃድ ይሁን፡፡

መጋቤ ሐዲስ ኀይለ እግዚእ አሰፋ

በትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ዋና ሐላፊ

“ስፉሐ ይኩን ትምህርትክሙ ከመ መንጦላዕት”

ከዚህ ይቆየን፡፡

ሐምሌ 6 ቀን 2018 ዓ.ም

አዲስ አበባ፡ ኢትዮጵያ፡፡