የ2019 ዓ/ም የሥርዓተ ትምህርት ማስተግበሪያ የጊዜ ሰሌዳ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት ከቅዱስ ሲኖዶስ በተሰጠው ተልዕኮ በሀገር ውስጥ እና ከሀገር ውጭ የሚገኙ ሕፃናት፣ ወጣቶች እና ጎልማሶችን በኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ሃይማኖት የጸኑ፣ ሥነ ምግባራቸው ያማረ፣ ቀደምት አባቶቻቸውን በመምሰል ቤተ ክርስቲያንን የሚረከቡ እና ሀገርን የሚጠብቁ ትውልድን የማፍራት ሥራውን በመሥራት ላይ ይገኛል፡፡

ይህንንም ከተዥጎረጎረ እና ወጥነት ከጎደለው፣ ለአንድ ዓላማና ግብ የተናጠል ሩጫ ከበዛበት አሠራር ሰንበት ትምህርት ቤቶቻችን ተላቀው በዓለም ዙሪያ የሚገኙ የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች በአንድ ሐሳብና በአንድ ቃል እንዲጓዙ የሚያስችል ሥራን በመሥራት ላይ ይገኛል፡፡

ከነዚህም አንዱና ዋነኛው የሰንበት ትምህርት ቤቶች ሥርዓተ ትምህርት ነው፡፡ ይህም ሥርዓተ ትምህርት በሀገር ውስጥም ሆነ ከሀገር ውጭ ባሉ አህጉረ ስብከት በትግበራ ላይ ይገኛል። ሰንበት ትምህርት ቤቶችም ለአተገባበር ያመቻቸው ዘንድ ዓመታዊ የትምህርት መርሐ ግብር የሚያስፈልግ በመሆኑ በሀገር ዐቀፍ ደረጃ ይህን ማስተገበሪያ ሰነድ ማዘጋጀት አስፈላጊ ሆኗል። ይህም ዓመታዊ የትምህርት ማስተግበርያ ሰነድ ለ2019 ዓ/ም የትምህርት ዘመን እንዲሆን ተደርጎ ተዘጋጅቷል፡፡

በዚህ ማስተግበርያ ሰነድ ውስጥ የዓመቱን የትምህርት መርሐ ግብር መጀመርያ እና መጨረሻ ጊዜ፣ የፈተና መርሐ ግብራት፣ የሴሚስተር የሪፖርት ጊዜያትን፣ የመርጃ መሣርያ ዝግጅትን ወዘተ በዝርዝር የያዘ ነው፡፡ ለዚህም የትምህርት መርሐ ግብር የየአህጉረ ስብከት ሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት እንዲሁም አጥቢያ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ሓላፊነታቸውን በአግባቡ በመወጣት ሰፊውን ድርሻ መያዝ ይጠበቅባቸዋል፡፡ ይህ የትግበራ ሰነድ ወይም የትምህርት መርሐ ግብር በተቀመጠለት ጊዜና ሰዓት ተፈጻሚ መደረግ ይኖርበታል።
ሰነዱን በዚህ ማስፈንጠሪያ ማግኘት ይችላሉ።

የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት
ሐምሌ 2018 ዓ/ም