ወቅታዊ መልእክት

ወቅታዊ መልእክት

ግንቦት ፯ ቀን ፳፻፲ወ፯ ዓ.ም

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት !!
በቅድሚያ ብፁዕ ወቅዱስ አባታችን ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት እንኳን ለ፳፻፲ወ፯ ዓ.ም የቅዱስ ሲኖዶስ ርክበ ካህናት ምልዓተ ጉባኤ በሰላምና በጤና አደረሳችሁ። በመንፈስ ቅዱስ አጋዥነት ለቤተ ክርስቲያን ጠቃሚ የሆነ ውይይት እንድታከናውኑ የልጅነት ጸሎታችን ነው።
የቅዱስ ሲኖዶስ ርክበ ካህናት ምልዓተ ጉባኤ የሚወያይበትን አጀንዳ ተመልክተነዋል። የተያዘውም አጀንዳ ጠቃሚ እንደሆነ ተረድተናል። ነገር ግን አሁን የቤተ ክርስቲያን አስተዳደር ላይ የሚስተዋሉ ቁልፍ መፍትሔ የሚሹ ጉዳዮች ለውይይት ቀርበዋል ብለን አናምንም። ምክንያቱም ከአጥቢያ እስከ መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ድረስ የሚስተዋሉ፤ በቅዱስ ሲኖዶስ በቁርጠኝነት ዘላቂ መፍትሔ ሊበጅላቸው የሚገቡ ዘርፈ ብዙ አስተዳደራዊ እና ተያያዥ ጉዳዮች ለውይይት ሳይቀርቡ ታልፈዋል።
በመሆኑም በሀገር አቀፍ ደረጃ ተለይተው፣ በማስረጃ ዳብረው እና በመጨረሻም ግንቦት ፮ ቀን ፳፻፲ወ፯ ዓ.ም የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ከበርካታ አህጉረ ስብከት ከተውጣጡ የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት አመራር አባላት እና ከአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ከተውጣጡ የክፍለ ከተማ ሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት አመራሮች፣ የገዳማት እና አድባራት ሰንበት ት/ቤት ሊቃነ መናብርት ጋር በአካልና በቴክኖሎጂ በመታገዝ ሰፊ ውይይት ተደርጓል። በመሆኑም በአካልና በቴክኖሎጂ በአመራሮች ውይይት የተደረገባቸው፤ የጋራ አቋም የተያዘባቸው እንዲሁም በቀጥታ የኦርቶዶክሳዊያን ምእመናንና ምእመናት ጥያቄም ጭምር የሆኑትን፤ እኛ የነገይቱ ቤተ ክርስቲያን ተረካቢ ወጣቶች በልጅነት አንደበት እንደሚከተለው ለማቅረብ እንወዳለን ።
እነርሱም፦
1. የቤተ ክርስቲያንን ሲኖዶሳዊ ልዕልና እና አንድነትን ማስጠበቅ ፤
ሀ. ታላቂቱ ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ከትናንቱ ይልቅ ዛሬ ተቋማዊ ህልውናዋ እና ልዕልናዋ አስጊ ደረጃ ላይ የሚገኝ በመሆኑ ቅዱስ ሲኖዶስ ሕገ ቤተ ክርስቲያን እና መዋቅራዊ አሠራርን በመፈተሽ እና በማስጠበቅ የቤተ ክርስቲያንን ሁለንተናዊ ፈተና በፍጥነት ሊያስቆም ይገባል፡፡
ለ. በነገረ ሃይማኖት ላይ እየተሰነዘሩ ያሉ ሐሰተኛ ትምህርቶች ቤተ ክርስቲያን የጠራ ትምህርቷን በተገቢው ሁኔታ፣ በሚገባው ዐውድ እና በሚመለከተው አካል ምላሽ እንዲሰጥባቸው፤
ሐ. ሐሰተኛ ትምህርት ያስተላለፉ ከመምህራን እስከ ሊቃነ ጳጳሳት ያሉ አካላት ላይ ተገቢው ቀኖናዊ ሥራ እንዲሠራ፤
መ. እየተድበሰበሰ ያለው የነገረ ቅብዓት ጉዳይ የማያዳግም እልባት ሊሰጠው ይገባል።
ሠ. በትግራይ ክልል የሚገኙ ኦርቶዶክሳዊያን ነፍስ ጉዳይ በእጅጉ ያሳስበናል። በክልሉ ከሚገኙ አህጉረ ስብከት አስተዳደራዊ ግንኙነት መቋረጥ እና እስከ አሁንም ይኽ ችግር ተገቢ የኾነ መፍትሔ ባለማግኘቱ፤ መለያየቱ ሥር ሰዶ፤ የጥፋቱ ጉዳት እየጨመረ እና የቤተ ክርስቲያኒቱን አንድነት ለማይፈልጉ አካላት ሰርግና ምላሽ ሆኖ ነፍሳት በኑፋቄ እየተነጠቁ ይገኛሉ። ከተፈጠረው የአስተዳድር ልዩነት በኋላ የተስተዋሉ የኑፋቄ እና ስልታዊ ጥፋትን አስመልክቶ ያዘጋጀነውን ዝርዝር የማስረጃ ሰነድ ለቋሚ ሲኖዶስና ለቅዱስ ፓትርያርኩ ብናቀርብም ተጨባጭ ምላሽ አልተሰጠም። በመሆኑም በትግራይ ያለ ኦርቶዶክሳዊ ምእመን በሚያስደነግጥ ፍጥነት በኑፋቄ እየተነጠቀ መሆኑን በመረዳት ልዩ ትኩረት ተሰጥቶት አስቸኳይ መፍትሔ ካልተሰጠው በፈጣሪ ፊት፣ በኅሊና እና በታሪክ ያስጠይቃል። አደገኛ ሰብራትም የሚያስከትል በመሆኑ አፋጣኝ መፍትሔ እንዲሠጥበት፤
ረ. በኦሮሚያ ክልል በሚገኙ አህጉረ ስብከት ወቅታዊ ችግር፣ ሌሎች የከረሙ አስተዳደራዊ ችግሮች እና ተያያዥ ምክንያቶች አብያተ ክርስቲያናት እየተዘጉ አገልጋይ ካህናት እና ተከታይ ምእመናን ወደ ሌላ እየፈለሱ እና እየተሰደዱ መሆናቸው የሚታይ የአደባባይ ሐቅ ነው። ይኸንኑ ችግር በጥናት ላይ ተመሥርቶ ከመመለስ ይልቅ ጳጳስ በመሾም ጥያቄዎቹ እንደተመለሱ የመቁጠር ከፍተኛ ዝንባሌ ተስተውሏል። በእርግጥ እርሱም ውጤታማ አይደለም። ችግሩን ከሥሩ ተረድቶ ምላሽ ባለመሰጠቱ የክልሉን ኦርቶዶክሳዊ በሌላ ዐውቅልሀለው ባይ አካል እንዲናወጽ ሆኗል:: በቅዱስ ሲኖዶሱም ለቋንቋዎች አገልግሎት የተመደበው በጀት እዚህ ግባ የሚባል ሥራ ሲሠራበት አልታየም። በአጠቃላይ በክልሉ የሚገኘውን የቤተ ክርስቲያኒቱን አገልግሎት በማጠናከር የሚፈለገውን ውጤት ለማምጣት የካህናት ማሠልጠኛ ማዕከላትን ማስፋፋት፣ መምህራንና አገልጋዮችን በማፍራት ተደራሽነትን የማስፋት ተጨባጭ ሥራ መሥራት ይገባል።
2. የቤተ ክርስቲያን አስተዳደራዊ ችግሮችን (ለጥፋት የዳረገንን ብልሹ አሠራርን) በተመለከተ፦
የሰበካ መንፈሳዊ ሥራ አስፈጻሚ ፣ ጠቅላላ ጉባኤ እና ከመንፈሳዊ ዘርፍ ውጪ ያሉ አስተዳደራዊ ጉዳዮች በቃለ ዐዋዲው እና በተገቢው የዘርፉ ባለሙያ እንዲመሩ አለማድረግ ለጥፋት እና ለብልሹ አሠራር ዳርጎናል።
ታላቂቱን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ከማይመጥን እና ብዙ ዋጋ ካስከፈላት አስተዳደራዊ ድክመት በመላቀቅ እና ዘመኑን በመዋጀት እናት ቤተ ክርስቲያንን መታደግ ለነገ የማያድር ሥራ ነው ። በመሆኑም :-
ሀ. የቤተ ክርስቲያን መንፈሳዊ አገልግሎት ተደራሽ እንዳይሆን፣ የምእመናን ነፍስ እንዲነጠቅ፣ የኢኮኖሚ አስተዋጽዖዋ እንዲደበዝዝ ፣ ተሰሚነቷና ተቀባይነቷ ጥያቄ ውስጥ እንዲገባ ምክንያት የሆነው በብቁ የአስተዳደር ባለሙያ የመፈጸም ችግር የገነገነ ነው። መንፈሳዊ ዕውቅት ብቻ ባላቸው ነገር ግን የአስተዳደር ክህሎት በሌላቸው፣ ዘመኑን የመዋጀት ክፍተት ባለባቸው ሊቃነ ጳጳሳት እና በዘመድ አዝማድ ደጅ ጥናት ሙያ ሳይኖራቸው በተመደቡ ሓላፊዎች መመራቱ ዋናው የችግሩ አካል ስለሆነ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ጠቅላይ ሥራ አስኪያጅነት፣ የአህጉረ ስብከት ጽ/ቤቶች የአስተዳደር ዘርፍ ከሊቃነ ጳጳሳት ውጪ በብቁ ባለሙያዎች እንዲመሩ እና ሊቃነ ጳጳሳት በሕግ አውጪነት እና ቤተ ክርስቲያንን በመጠበቅ ፤ ቤተ ክርስቲያንን እንዲመሩ፤ሕገ ቤተ ክርስቲያን ላይ ማሻሻያ ማድረግ ይገባል ::
ለ. በሕገ ቤተ ክርስቲያን እና በቃለ ዐዋዲ የተደነገገው የሰበካ ጉባኤ የአስፈጻሚነት እና የሰበካ መንፈሳዊ ጠቅላላ ጉባኤያት ሚና መገሰስ ፦ በቃለ ዐዋዲው የተደነገገው የካህናት፣ የምእመናን እና የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች የአስፈጻሚነት ተሳትፎ ማለትም በወረዳ ቤተ ክህነት፣ በሀገረ ስብከት መንበረ ጵጵስና እና በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ተግባራዊ እንዳይደረግ ተገፍቷል። በዚህም ምክንያት የክፍል እና የመምሪያ ሓላፊዎች በቤተ ክርስቲያን ሕግ በግልጽ ከተደነገገው ከሦስቱ አካላት ተዋጽዖ ውጪ በሕግ የማይታወቅ የመደበኛ ቅጥር ሠራተኞች ስብስብ ” የአስተዳደር ጉባኤ ” የሚባል መሥርተው ቤተ ክርስቲያኒቱን እየበደሉ ይገኛሉ። ካህናት፣ ምእመናን ፣ የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች የአስፈፃሚነት ሚናቸውን እንዲወጡ በሕገ ወጥ ስብስብ የተነጠቀው የአስፈጻሚነት ድርሻ በየመዋቅሩ ያለ ምንም ቅድመ ሁኔታ ተመልሶ ተግባራዊ ሊደረግ ይገባል ።
ሐ. የሀብት ብክነት፦ ንጽሕናን ገንዘብ ያደረጉ አባቶቻችን ለስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ ብለው የገነቧቸው እና ለአገልግሎት ያበቋቸውን ሕንፃዎች ፣ ድርጅቶች እና ቤቶች ዛሬ በአያያዝና በቁጥጥር ሥርዓት ጉድለት ከፍተኛ ዘርፋና ግፍ የሚፈፀምባቸው ሆነዋል፤ ለብክነትም ተዳርገዋል። ለዚህም ጤናማ የሥራ አፈፃፀም ታሪክ የሌላቸው አካላት እየተፈራረቁ የመዘበሩት የቤቶች ድርጅት አንዱ ማሳያ ነው። ከአጥቢያ ጀምሮ በዘመናዊ አስተዳደር እጦት ምክንያት ለኪራይ አገልግሎት የዋሉ ሕንፃዎች ፣ ቤቶች እና ይዞታዎች በረቀቀ የሙስና ስልት ከሚጠበቅባቸው ገቢ በታች እየሰበሰቡ አብላጫውን አስተዳዳሪ ተብለው በሚሾሙ አካላት ይዘረፋሉ። በመሆኑም አሁን ላይ የአጥቢያዎች ቁመና የሠራተኞች ደሞዝ መክፈል ላይ ብቻ ተቸክሎ የምእመናን ሕይወት፣ ስብከተ ወንጌል ማስፋፋትና ልማት የማይታሰብ ሆኗል።
በመሆኑም ለወንጌል ልማት መዋል የሚገባው ሀብት ለምዝበራ ተዳርጓል። ቤተ ክርስቲያን መንፈንሳዊ ዕውቀትን ከዘመናዊው ዕውቀት ጋር ያጣመሩ ፈሪሐ እግዚአብሔር ያላቸው ልጆች የሌሏት ይመስል፤ የለየላቸው ጨካኝ ወንበዴዎች የሚቀራመቷት ሆናለች። በአያያዝ እና በብቁ አስተዳደር እጦት ሀብቷ ለብክነት ተዳርጓል ፤ ለጥቅመኞችም ሲሳይ ሆኗል።
ይህን የአደባባይ ምሥጢር መፍትሔ ከመስጠት ይልቅ አይቶ እንዳላየ፤ ሰምቶ እንዳልሰማ ማለፍ ቤተ ክርስቲያንን ለወንበዴዎች አሳልፎ መስጠት ነውና በቁርጠኝነት ሥር ነቀል ለውጥ ሊደረግ ይገባል።
መ. ከአጥቢያ ጀምሮ በሁሉም መዋቅር ዘመኑን የዋጀ የአስተዳደር ፣ የፋይናስ የግምገማ ፣ የቁጥጥር እና የምዘና ሥርዓት አለመኖር :- በሁሉም መዋቅር የሥራ ግምገማ ፣ የሥራ አፈጻጸም እና የሀብት አጠቃቀም ቁጥጥር ሥርዓት የለም። አጥፊ አይጠየቅም፤ በአጥፊዎች ላይ ቀኖና ቤተ ክርስቲያን አይተገበርም፤ ሹመት፣ ዕድገት፣ ዝውውር ያለ ምዘና ሥርዓት በዘፈቀደ ይከናወናል። የሠራተኞች የሥራ መደብ በከፍተኛ የብር መጠን ይቸበቸባል ፤ ሌብነት ፣ ሥርዓት አልበኝነት ነግሠው መንፈሳዊነት ከቦታው ጭራሹኑ ጠፍቷል። የሥራ ዋስትና የለም፤ ከኢአማኒያን እንኳ በማይጠበቅ መልኩ የካህናት፣ የዲያቆናት እና የስብከተ ወንጌል የሥራ መደብ ላይ የአየር ላይ ሽያጭ ፣ የወንዘኝነት መጠቃቀም የመሳሰሉት ዘግናኝ የግፍ ግፎች ይፈጸማሉ። ይህ ችግር በብዙ ሀገረ ስብከቶች መጠኑ ይነስም ይብዛ የሚስተዋል ሲሆን በተለይ ዋነኛ መገለጫው የሆነው እንደ አዲስ አበባ ባለ ሀገረ ስብከት ጎልቶ ይታያል። እንደ ማሳያ በተለያየ ጊዜ የተሾሙ ብፁዓን አባቶችም ሆነ በተለያየ እርከን ያሉ ሓላፊዎች የግላቸው የአሠራር ችግር እንደተጠበቀ ሆኖ አንዱ የችግሩ ምንጭ እንደ ሲኖዶስ አብረው የሚወስኑ ጥቂት የማይባሉ ሊቃነ ጳጳሳት ቅጠርልኝ፤ አዛውርልኝ፣ መድብልኝ፣ አታዘዋውርብኝ፣ አትቅጣብኝ የሚሉ ጫናዎች እንደሚያሳድሩባቸው ሁሉም በሚባል ደረጃ የሚገልጹት ለተበላሸ አሠራር ምክንያት ሆኗል። በመሆኑም ይህ የመልካም አስተዳደር እንዲሰፍን የቅዱስ ሲኖዶስ ቁርጠኛ አቋም ከሆነ አባቶች ለወዳጅ ዘመድ የሚያደርጉትን ጣልቃ ገብነት ማስቆም ያስፈልጋል ።
ረ. ውስን ሊቃነ ጳጳሳት በእርግና ምክንያት በግልፅ አስተዳደራዊ ሥራ ማከናወን እንደማይችሉ እየተስተዋለ ስለ ነፍሳቱ እረኛ ማጣት ደንታ ቢስ በመሆን መፍትሔ ሳይሰጥ ቀርቷል፤ እንዲሁም ቁጥራቸው ጥቂት ቢሆንም ሊቃነ ጳጳሳት ከምእመናን ጋር እሰጥ አገባ ውስጥ ገብተው ሀገረ ስብከቱ ታውኮ፤ ምእመናን አዝነው እና ከበረቱ ተገፍተው ወጥተው ሲቀሩ ሲኖዶስ በዝምታ ተመልክቶታል። ሀገረ ስብከታቸውን በሚገባ በማያስተዳድሩ ሊቃነ ጳጳሳት ላይ ሕገ ቤተ ክርስቲያን ላይ በተደነገገው መሠረት አስተዳደራዊ እርምጃ አለመወሰዱ እና የበዛ ዳተኝነቱ ቤተ ክርስቲያንን ክፉኛ ጎድቷታል። በመሆኑም በእርግና ላይ ለሚገኙ ብፁዓን አባቶች ረዳት መሾም ፣ የታወቀ የአስተዳድር ድክመት ያለባቸውን አባቶች ተገቢውን የተጠያቂነት አሠራር በተግባር ላይ ማዋል ይገባል።
ሸ. በመንፈሳዊ አገልገሎት ማለትም በፍትሐት፣ በሥርዓተ ተክሊልና በሥርዓተ ቀብር ላይ ከመንፈሳዊ አሠራር ያፈነገጠ የለየለት ንግድ ምእመናንን አስመርሯል። በቅዳሴ ሰዓትና አገልግሎት፣ ማሕሌት፣ ሰዓታት እና በሌሎች መንፈሳዊ አገልገሎቶች ላይ እየተሰተዋለ ያለው ከመጻሕፍትም ከአባቶችም ያላገኘነው ዐዲስ ባዕድ ልምምድ ተበራክቷ ። በፍቅር እና በረከትን ሽቶ ማገልገል ሞኝነት መስሎ፤ ከመንፈስ ቅዱስ አሠራር ውጪ እንደ መደበኛ ሥራ የማየትና ከፍቅር ይልቅ በሥራ መንፈስ የማገልገል አዝማሚያ መፍትሔ ሊፈለግለት ይገባል።
ከ. በከተማ ልማት እና መስፋፋት ምክንያት ምእመናን ከአምልኮ ሥፍራ እንዳይለዩ እና አድባራቱና ገዳማቱ ተገልጋይ እንዳያጡ፣ ዘመኑ በመዋጀት ከአምልኮ ሥፍራና መልሶ ማልማት ጋር የተጣጣማሙ ስልታዊ የተቀናጁ የልማት ፕሮጀክቶችን በማዘጋጀት በአድባራቱ ቦታ እና ከመንግሥት ቦታን በመጠየቅ ምእመናን ተኮር የልማት ሥራ መሥራት ምእመናን ከቀያቸው ሣይርቁ አምልኮተ እግዚአብሔርን መፈጸም ያስችላቸዋል። በመሆኑም ነገን አሻግሮ በመመልከት ዛሬ ላይ ወደ ሥራ መግባት ይገባል።
3. የሥነ ምግባር ግድፈት ክብረ ክህነት፣ ክብረ ምንኩስናን የሚያስነቅፍ የተገለጠ የቀኖና ጥሰት መበራከት:-
የታወቀ፣ የተገለጠ የሥነ ምግባር ግድፈቱ ትውልዱን ከቤተ ክርስቲያን እያራቀው ነው። ትናንት ለቀሳውስት እና ለሊቃነ ጳጳሳት የሚሰጠው ክብር ተሸርሽሮ ጀርባ መሥጠት ተጀምሯል። በከተማ መነኮሳት እና መነኮሳይያት ኢክርስቲያናዊ ምግባር ምእመናንና ወጣቱን የማያንጽ አሰናካይ፤ ከሥርዓተ አበው፣ ከሥርዓት ምንኩስና ያፈነገጠ አሳፋሪ ልምምድ ተበራክቷል።
መንፈሳዊ ሕይወት ተዘንግቶ ፤ ቦታ ተነፍጐት ዓለማዊነትና ሥጋዊ ፍላጎት ነግሧል። ከታወቀ ደሞዝ በላይ ኑሮ ፤ ምንጩ የማይታወቅ፤ ተንቀሳቃሽና የማይንቀሳቀስ ንብረት ማካበት፣ ከገዳማት እና አድባራት ሠራተኛ እስከ ሊቃነ ጳጳሳት ድረስ ሕጋዊ እስኪመስል በአደባባይ ተገልጧል። ይኸ አደገኛ በሽታ መፍትሔ ሊሰጠው ይገባል፤ ባለቤት የሌለው ይመስል ልቅ የሆነውን ጉዳይ ከሊቃነ ጳጳሳት ጀምሮ ሁሉም በየተዋረዱ ለሥነ ምግባር ጥሰቱ ተጠያቂነት የሚሰፍንበት ሥርዓት ሊበጅለት ይገባል ።
4. በሀገራዊና ዓለም አቀፍ ጉዳይ ላይ ተሳትፎን በተመለከተ
ሀ. በሀገር ግንባታ፣ በሰላም እና እርቅ ክዋኔ የካበተ እና ተጠባቂ ልምድ እና አስተዋጽዖ ያላት ቤተ ክርስቲያን ፣ በሊቃውንቷ አዎንታዊ አስተዋጽዎ ማበርከት ሲገባት በግልጽ፤ ከታወቀው አዎንታዊ ሚናዋ ተናጥባለች። በየዕለቱ የሂስና ግለሂስ አስተምህሮን የምትተገበር ቤተ ክርስቲያን ፣ በጸሎትና በውይይት ችግሮች የመሻገር ሰፊ ልምድ ያላት ቤተ ክርስቲያን፤ ከባለ ድርሻ አካላት ጋር ያላትን ግንኙነት በጥበብ በማስኬድ፣ በውይይት ፣ በምልዐት በመመካከር ማስኬድ ይገባታል። በሀገራዊ ጉዳይ ተቋማዊ ተሳትፎና ድርሻን መወጣት ዐቢይ ተግባር መጠናከር ይገባል ።
ለ. በመንግሥት በኩል እየተዘጋጁ ባሉ ልዩ ልዩ ረቂቅ አዋጆች፣ ደንቦችና መመሪያዎች ላይ ተገቢነት ያለው ተቋማዊ ተሳትፎን በማጠናከር፤ ልዩ ልዩ ረቂቅ የሕግ ፣ የደንብ ዝግጅቶች ላይ መሳተፍ፣ ክትትል ማድረግ እነዚህ መመሪያዎች ከመውጣታቸው አስቀድሞ በቤተ ክርስቲያኒቱና በአማኞቿ ላይ የሚያመጣውን በጎም ይሁን ክፉ ተጽእኖ በባለቤትነት መንፈስ በመመርመር ተገቢነት ያለው ሱታፌ እንዲኖራት የሚያስችል አግባብነት ያለው የውክልና ተሳትፎዎች ማድረግ እንድትችል በባለ ሙያዎች በተደራጀ ቡድን ክትትል እና ተቋማዊ ተሳትፎ ሊጠናከር ይገባል።
ሐ . በሀገራችን የሚፈጠሩ ችግሮች እንዲፈቱ እና ሀገራዊ ሰላም እንዲረጋገጥ አዎንታዊ የቤተ ክርስቲያን ሚናን በተመለከተ ፦ ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን በሀገራዊ ሰላም ፣ በህዝቦች ስደት፣ ሞት እና አለመረጋጋት ዙሪያ ፤ አስቀድሞ ለዘመናት መገለጫዋ ከሆነው ልምዷ በመነሣት ችግሩ እንዲቀረፍ ፍሬ ያለው ተግባር አልተከናወነም:: ከመግለጫ በዘለለ የተቀናጀ ፣ ውጤት ሊያመጣ የሚችል አዎንታዊ ሚናዋ ደብዝዟል። በመሆኑም ችግሩን ከመቅረፍ እና በወንድማማቾች መሀል የተፈጠረን ልዩነት በማጥበብ ሀገራዊ ሰላም እንዲሰፍን ቤተ ክርስቲያን ተጠባቂ ሚናዋን ከመወጣት አንፃር ሰፊ ሥራ ይጠበቃል ፡፡
መ. ቤተ ክርስቲያን ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በዓለም አቀፍ የሃይማኖት እና ሰብዓዊ ክዋኔዎች ላይ በአግባቡ አለመሳተፍ፤ በአኃት አብያተ ክርስቲያናት መደበኛ እና ልዩ ልዩ ጉባኤያት አለመወከል እንዲሁም ከባለ ድርሻ አካላት ጋር ተገቢውን ተሳትፎ እና መብቷን የማስከበር ሥራዎች አለማከናወን ይስተዋላል:: ቅዱስ ፓትርያርኩ ከሀገር አቀፍ እና ዓለም አቀፍ ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርቲያን ከምትወከልበት መድረክ መሄድ ካቋረጡ ሰነበቱ። በመሆኑም ይኸ ታላቋን ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስትያን የማይመጥን ድርጊት ተገቢው ማስተካከያ ሊሰጠው ይገባል።
ከላይ በዝርዝር የተገለጠው በዋነኛነት የብልሹ አስተዳደር ውጤት፤ ቤተ ክርስቲያን መንፈሳዊ አገልግሎቷን እንዳታስፋፋ፣፤የነፍስ ድኅነትን እንዳታውጅ፤ መንግሥተ እግዚአብሔርን እንዳትሰብክ እንቅፋት የሆነ፤ ነፍሳትን ከበረቱ ያስኮበለለ፤ የቀሩትም ለቀቢፀ ተስፋ የዳረገ በመሆኑ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ፤ ከአሁኑ የከፋ ጥፋት ሳይከሰት ሥር ነቀል መፍትሔ በመሥጠት እና የምእመናንን የአስፈፃሚነት ሱታፌ በማረጋገጥ የምንረከባትን ቤተ ክርስቲያን እንዲታደግልን እና ሐዋርያዊ አደራውን እንዲወጣ በልጅነት መንፈስ ዝቅ ብለን እንማፀናለን ።
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
የሰ/ት/ቤቶች አንድነት የማኅበራዊ የትስስር ገጾችን ቤተሰብ ይሁኑ!
(የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት)
ወቅታዊ መልእክት

ወቅታዊ መልእክት

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ (ሀገር አቀፍ) የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ከውጪና ከውስጥ የሚቃጡባትን ፈተናዎች በመቋቋም ከውጭ የሚቃጡባትን ፈተናዎች ሰማዕትነትን በሚቀበሉ ልጆቿ ምስክርነት፣ ምንፍቅናን በቃል የመጣውን በቃል በመጻሕፍት የመጣውን በመጻሕፍት በመመከት ሐዋርያዊ ቅብሎሿን ጠብቃ መሠረተ እምነቷን፣ ዶግማና ቀኖናዋን ቅዱስ ትውፊቷን ለትውልዱ እያስተማረች ጸንታ ቆይታለች፤ ወደ ፊትም ትኖራለች፡፡

ቤተ ክርስቲያናችን ዛሬ በልዩ ልዩ ውጫዊ ፈተናዎች ዋጋ እየከፈለች ያለች ቢሆንም ከሁሉ የከፋው ግን ከክብር በላይ የላቀ ክብር ባጎናጸፈቻቸውና እረኛና ጠባቂ እንዲሆኑ ባሰማራቻቸው ልጆቿ በተደጋጋሚ እየገጠማት ያለው የቀኖና ጥሰት ነው። የጥር ፲፬ ጳጳሳት ሹመት፣ የትግራይ ሲኖዶስ፣ የቅባት ጳጳሳት ሹመት ፤ ፖለቲካን ተጠግቶ ቤተክርስቲያንን የማጥቃት ክፉ ግብር ሳያንሳት ፤በተገኘው አጋጣሚ ኹሉ የምንፍቅና ትምህርቶች የሚያስተላፉትን በዝምታ መመልከት እየበዛና በዚህም በጎቿን ከበረቷ ለማስነጠቅ ለሚሠሩ ሁሉ ተባባሪ በመሆን የሚኬድበት ርቀት ቤተክርስቲያኒቱን ዋጋ እያስከፈለ በመሆኑ በቃ ሊባል ይገባዋል፡፡ ለማሳያ ይሆን ዘንድ በአቡነ በርናባስ መባልእትንና ነገረ ክርስቶስን አስመልክቶ፤ በአቡነ ፊልጶስ እመቤታችንና ሥላሴን አስመልክቶ የተናገሩትን የስሕተት ትምህርቶች ቅዱስ ሲኖዶስም ሆነ የሊቃውንት ጉባኤ በወቅቱ ማስጠንቀቂያም ሆነ የእርምት እርምጃ ባለመውሰዳቸው ዛሬ በአቡነ ገብርኤል እመቤታችንንና ነገረ ክርስቶስን አስመልክቶ ያውም በዐውደ ምሕረት፣ እንዲሁም በዕለተ ስቅለት በተደረገ የአዳራሽ ጉባኤ ለተናገሩት የኑፋቄ ትምህርት አድርሶናል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ቤተ ክርስቲያን ገፊ እንደሆነች እና ስለክርስቶስ የሚዘምሩትን እንደምታባርር እርሷም ስለ ክርስቶስ እንደማትዘምር በአደባባይ በጉባኤ ያለምንም ፍርሀት ሲናገሩ ተደምጠዋል፡፡

ከዚህም ባለፈ የማኅበራት ምዝገባ ክትትልና ቁጥጥር መምሪያን ጨምሮ የተለያዩ ሊቃነ ጳጳሳት በኑፋቄ ትምህርት ማስፋፋት ላይ የተሰማራውን “ፍኖተ ጽድቅ” ማኅበርን በገንዘቡ በሚሠራቸው የስቱዲዮ ግንባታ፣ የመጽሐፍ ኅትመት እና የመሳሰሉት ተግባራት በመማረክ የቤተክርስቲያንን ክብር አሳልፈው ሰጥተዋል፡፡ በዚህ ሂደት ላይ አንዳንድ መምህራን እና ማኅበራትም ተሳታፊ መሆናቸው በእጅጉ አሳዛኝ ነው፡፡

ይህ እንዲሆን ምክንያት ከሆኑ ነገሮች መካከል የሚከተሉት በዋናነት ተጠቃሽ ናቸው።

1. የአስተዳደር ብልሹነት የወለደው ዘርፈ ብዙ ችግር
በእኛ መረዳት አሁናዊው ፈተና እና ችግር ከውጪያዊው የዝግጅት ጥቃትና ፈተናም በላይ የበረታው የውስጥ ችግር ነው። ለዚህም ዋናውና አንደኛው የሁለንተናዊ ድካማችን ምክንያት የቤተ ክህነቱ ብልሹ አስተዳደር ነው።
አሁን ላይ ያለው የቤተ ክህነት አስተዳደር ዘመኑን በመዋጀት የቤተ ክርስቲያንን መንፈሳዊ ተልዕኮ በማስፈፀም ነፍሳትን ለመንግሥተ እግዚአብሔር ለማብቃት የሚያስችል ቁመና እና ብቃት ላይ አይገኝም ። ሕግ አውጪ፣ ሕግ ፈፃሚ እና ሕግ ተርጓሚ አንድ አካል በመሆን፣ ተጠቅልሎ በተያዘ ሥልጣን ቤተ ክርስቲያኒቱ እጅ ተወርች ተቀፍድዳ ወደ ትውልዱ እንዳትደርስ እየተሠራ ይመስላል።

ቤተ ክርስቲያን በማይመጥናት ደካማ አስተዳደር ምክንያት ከተመሠረተችበት ነፍስ የማዳን መንፈሳዊ ተግባር ተናጥባለች። አስተዳደሩ ምእመናንን ለመንፈሳዊ ፍሬ ከማብቃት ይልቅ ለውድቀታቸው ምክንያት ሆኗል። በተለያዩ ጊዜያት ተጠንተው የቀረቡ ልዩ ልዩ የአስተዳደር ማሻሻያዎች እየተኮላሹ ጉዞው ከድጡ ወደ ማጡ ሆኗል:: በ ፳፻ወ፬ ዓ.ም ለሲኖዶስ የቀረበው የመሪ ዕቅድ ትግበራ ጥያቄ ፲፫ ዓመታት ሲገፋ ቆይቶ አሁንም ቦታ ተነፍጐታል። አስተዳደራዊ ለውጥ ጠልነቱ ተባብሶ ቀጥሏል። እኔ ብቻ በሚሉ ፣ ቤተ ክርስቲያን እንደ ግል ተቋማቸው በሚያዩ አካላት ተወራለች:: በሃይማኖት ችግር ፣ በቀኖና ጥሰት እና በሙስና ተጠያቂ መሆን የሚገባቸው አካላት የተሻለ ሹመትና ሽልማት ይሰጣቸዋል፡፡

2. ለሊቃውንት ጉባኤ ትኩረት መነፈጉ
የሊቃውንት ጉባኤ ተገቢው ትኩረት ሳይሰጠው በመቅረቱ ፣ እንዲሁም ሊቃውንት ክብራቸው ባለመጠበቁ እና ከውሳኔ ሰጪነት ድርሻ በመገለላቸው ፤ ለስሑት ትምህርት በሚገባው መልኩ ምላሽ መስጠት የማይችል ሆኗል:: እንዲሁም በቤተክርስቲያኒቱ ስም ለሚታተሙና ለሚሰራጩ መጻሕፍትና ልዩ ልዩ የምስልና የድምፅ እንዲሁም የኅትመት ውጤቶች የመገምገምና ዕውቅና የመስጠት ሥልጣኑ ተነጥቋል። የአደረጃጀትና የመከላከል አቅሙ በመዳከሙ፤ በመዋቅሩ ውስጥ የተሰገሰጉ ሐሰተኛ መምህራን በአፍም በመጽሐፍም ስሁት ትምህርታቸውን በቤተ ክርስቲያኒቱ ዐውደ ምሕረት እያሰራጩ ይገኛሉ።

ትናንት አባቶች ያቆዩትን ሀብት መንዝሮ መጠቀም እንጂ የራሳቸውን አሻራ የማያኖሩ፣ ሀብት ንብረቷን ጠብቀው ከማቆየት ይልቅ ለግል መዝብረው ቀሪውን ለዘራፊ አሳልፈው የሰጡ ከመንፈሳዊ ክብር በጐደሉ፣ በሥጋ ሐሳብ ጨርሶውኑ በተወሰዱ፣ ምግባር በጎደላቸው ከአጥቢያ ጀምሮ እስከ ሊቃነ ጳጳሳት ድረስ ባሉ አገልጋዮች እየተፈተነች ትገኛለች።
ያለ ዋጋ ከሚሰጠው መንፈሳዊ ሹመት ጀምሮ የቤተ ክርስቲያንን መንፈሳዊ አገልግሎት የሚጎዳ እኩይ ተግባር በእጅ መንሻ የሚፈጽሙ አካላት በሁሉም መዋቅር ውስጥ ተሰግስገው ቤተ ክርስቲያን የተመሠረተችበትን ዓላማ እንዳታሳካ ሳንካ ሆነውባታል።

ስንዱዋ እመቤት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በሕግ እና በሥርዓት ዝግጅቷ እንከን አይወጣላትም። ነገር ግን ከሕግና ከሥርዓት ባፈነገጡ፣ ሐሰተኛ ትምህርት በሚያሰራጩ እና ኢ-ክርስቲያናዊ በሆነ ሕይወት ወስጥ በሚመላለሱ በተለይ በሁሉም መዋቅር ወስጥ በሚገኙ አገልጋይ ሠራተኞች ላይ ተግባራዊ ርምጃ አለመወሰዱ ለምእመናን ተስፋ መቁረጥ እና ፍልሰት ምክንያት ሆኗል።

3. በሕግ ከተሰጣቸው መብት ውጪ በማስተማር የሚሰማሩ ማኅበራትን በሕግ አግባብ ወደ መስመር አለማስገባት
የሰሞኑ ስሁት ትምህርት በሕጋዊ ዕውቅና ስም የሚንቀሳቀሱ ማኅበራት እኩይ ተግባር ከትናንት የቀጠለ የብልሹ አስተዳደር መገለጫ ነው። የማኅበራት አስተዳደር ደንብ ፀድቆ ሥራ ላይ ከመዋሉ በፊት ደንቡ ላይ የሚስተዋሉ ክፍተቶችን በማስረጃ በማስደገፍ የማሻሻያ ሐሳብ ብናቀርብም ተቀባይነት ሳያገኝ ቀርቷል። በመሆኑም የፈራነው ደርሶ ፤ ደንቡን ለማስፈፀም የተቀመጠው የማኅበራት ምዝገባ ክትትል እና ቁጥጥር መምሪያ፤ በማኅበራት አስተዳደር ደንብ አንቀጽ ፲ ላይ የማኅበራት ዓለማ “ለትምህርት ተጠሪ ተቋማት ድጋፍ መስጠት ነው” በሚል የተደነገገ ቢሆንም እንደ ‹‹ፍኖተ ጽድቅ›› ያለ ማኅበር ድጋፍ ሰጪ ሳይሆን ፈፃሚ ሆኖ፣ ማኅበሩ ከተመሠረተበት ዓላማ ውጭ ትምህርተ ወንጌልን በአዳራሽ ውስጥ ሲሰጥ፤ በሚዲያ ትምህርት ሲያስተላልፍ አልፎ ተርፎ የቤተ ክርስቲያን መዝሙሮቿን ከሥርዓቷና ከቀኖናዋ ውጪ በሆነ ሁኔታ በሚዲያ እያቀናበረ ሲያስተላልፍ ተገቢው አስተዳደራዊም ሆነ ቀኖናዊ እርምጃ እንዲወሰድ ከማድረግ ይልቅ በማኅበርነት በመመዝገብ እንዲሁም በደንቡ የተሰጠውን የመቆጣጠር ሓላፊነት የማኅበራት ማደራጃ ምዝገባ ክትትል እና ቁጥጥር መምሪያ ባለመወጣቱ ዛሬ ለደረሰው ስሑት ትምህርት ዝግጅትና ስርጭት አብቅቶናል፡፡
ይኽ ማኅበር ከኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አስተህምሮ ውጪ ስሑት ትምህርት የሚሰጥበት ተቋም እንደሆነ በተጨባጭ እየታወቀ እና በአካል ቀርበው አረጋግጠው እንኳን ቅዱስ ፓትርያርኩን በዚያ ሥፍራ እንዲገኙ በማድረግ ቤተ ክርስቲያንን አሳልፈው የሰጡ የቤተክርስቲያኒቱ አገልጋዮች መኖራቸው የአደባባይ ሐቅ ነው፡፡

በመሆኑም ከዚህ በታች የዘረዘርናቸው ትኩረት የሚሹ ጉዳዮች ተገቢው ትኩረት እንደሚሰጣቸው እና የእርምት እርምጃ እንደሚወሰድባቸው እናምናለን።

1. የሊቀ ጳጳሱ ኢ-ኦርቶዶክሳዊ አስተምህሮ በቅዱስ ሲኖዶስ ቀኖናዊ እርምጃ እንደሚወሰድበት ብናምንም በሚገባ እና በትኩረት ጉዳዩ እንዲታይና መፍትሔ እንዲሰጠው፡፡ እንዲሁም በተመሳሳይም ስሑት ትምህርቶችን የሚያስተምሩ እና ያስተማሩ ሌሎች ጳጳሳት እና መምህራን ጉዳይም አብሮ እንዲታይ፣ ይኽን አጋጣሚ ተጠቅሞ የሊቃውንት ጉባኤም በስሑት አስተምህሮዎች ላይ ተገቢውን ምላሽ እንዲሰጥ ቢደረግ፡፡

2. ሓላፊነቱን በአግባቡ ያልተወጣው የማኅበራት ምዝገባና ክትትል እና ቁጥጥር መምሪያ ከሊቀ ጳጳሱ ጀምሮ በየደረጃው ያሉ ሓላፊዎች እንዲጠየቁ፡፡

3. የማኅበራት ምዝገባ ክትትልና ቁጥጥር መምሪያ የዕውቅና ሰርተፊኬት ከመቸርቸር ወጥቶ፣ ደንቡና አሠራሩን ዳግመኛ በመፈተሽ፣ የዕውቅና አመዘጋገብ፣ ክትትልና ቁጥጥር ሒደቱም ንጥር ያለ እና መስፈርቶች የወጡለት እንዲሆን፡፡

4. ቅዱስ ፓትርያርኩን በማሳሳት ” ፍኖተ ጽድቅ ” በተባለው ማኅበር ዝግጅት ላይ እንዲገኙ ያደረጉ የቅዱስ ፓትርያርኩ ልዩ ጽ/ቤት ሓላፊና የፖትርያርኩ የፕሮቶኰል ሹም እንዲጠየቁ፡፡

5. ‹‹ፍኖተ ጽድቅ›› የተሰኘው ማኅበር በቤተክርስቲያን ላይ እያደረሰ ያለውን የተሐድሶ ኑፋቄ ትምህርት ባለማረሙ ምክንያት ማኅበሩ የምዝገባ ፈቃዱ ተሰርዞ ባስተላለፈው ትምህርቶች በቀኖና እንዲጠየቅ እና በዚሁ አጋጣሚ ከመምህራን እስከ ሊቃነ ጳጳሳት “ፍኖተ ጽድቅ” ከተባለ ማኅበር ጋር የጀመሩት በነዋይ ላይ የተመሠረተ ግንኙነት በአስቸኳይ እንዲቆም እንዲደረግ። እንዲሁም በቤተ ክህነቱ የበላይ ሓላፊዎች በኩል እናት ቤተ ክርስቲያናችን አንዳች ሳይጎድልባት ባልተገባ መሻት ከባለ ጸጋ እጅ ለማኝ በማድረግ ቅድስት ቤተክርስቲያንን የማዋረድ እና አሳልፎ የመስጠት እኩይ ተግባር እንዲቆም።

6. የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት ኦርቶዶክሳዊት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊ አገልግሎቷን እንዳታሰፋ እጅ ተወርች ቀፍድዶ የያዛት ደካማ፣ ብልሹ አስተዳደር እንዲስተካከል በልጅነት መንፈስ በተደጋጋሚ የችግሮቹን ማሳያና መፍትሔዎቹን፣ ሥርዓተ መዋቅርን በመጠበቅ እስከ ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ድረስ ቢያቀርብም ተጨበጭ ምላሽ አልተሰጠውም ። ይህም ጉዳይ ከግንዛቤ ገብቶ አፋጣኝ መፍትሔ ሊሰጠው ይገባል።

ነገር ግን አሁንም እንደ ቀድሞው ተሸፋፍኖ የሚታለፍ እና መፍትሔ ከመስጠት ይልቅ ታላቋን ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስትያን የማይመጥነው ብልሹ አስተዳደር የሚቀጥል ከሆነ በዓለም አቀፍ ደረጃ ከሚገኙ ሊቃውንት፣ ምእመናን፣ እና የሰንበት ት/ቤት አባላት ጋር በመሆን የምንረከባትን እና ለትውልድ የምናሰረክባትን እናት ቤተ ክርስቲያን የምንታደግበትን መንገድ የምንከተል መሆኑን በዚሁ አጋጣሚ ለመግለፅ እንወዳለን።

የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት
ሚያዚያ ፳፩ቀን ፳፻፲ወ፯ ዓ.ም
አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ

የሰ/ት/ቤቶች አንድነት የማኅበራዊ የትስስር ገጾችን ቤተሰብ ይሁኑ!

(የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት)

Youtube

https://www.youtube.com/@eotc-gssu

Facebook

https://www.facebook.com/gssu.eotc

Telegram

https://t.me/eotcgssu21

Tiktok

@eotc_gssu

“ኢሀሎ ዝየ ዳእሙ ተንሥአ በከመ ይቤ – ከዚህ የለም እንደ ተናገረው ተነሥቷል፡፡” ማቴ.28፡6

በጌታችን በመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መቃብር በራስጌና በግርጌ የነበሩ ቅዱሳን መላእክት ማልደው ወደ ጌታ መቃብር ለሄዱ ሴቶች ሕያውን ከሙታን መካከል ስለምን ትፈልጋላችሁ ከዚህ የለም እንደ ተናገረው ተነሥቷል በማለት መልሰውላቸዋል፡፡ ሴቶቹ ወደ መቃብሩ መሄድ የጌታችንን ሥጋ ሽቱ ለመቀባት ነበር፡፡ ነገር ግን እንደ ጠበቁት ሦስት ቀን የሞላው ጠረኑ የተቀየረ ሥጋ ሳይሆን ባዶ መቃብር ነበር ያገኙት፡፡ ማስተዋል አቅቷቸው እንጂ ጌታችን ከሞቱ አስቀድሞ “ይህንን ቤተ መቅደስ አፍርሱት በሦስተኛው ቀን አነሣዋለሁ” ብሎ በሥልጣኑ በሦስተኛው ቀን እንደሚነሣ ነግሯቸው ነበር፡፡ (ዮሐ.2፡18) በሌላም የወንጌል ክፍል “ያለ እኔ ፈቃድ ነፍሴን ከሥጋዬ የሚለያት የለም፤ እኔ ወድጄ እለያታለሁ እንጂ በመቃብር ላኖራት አዋሕጄም ላስነሣት ሥልጣን አለኝ፡፡” በማለት ስለሞቱና ስለ ትንሣኤው ተናግሮ ነበር፡፡ (ዮሐ.10፡18)

የጌታችን ሥጋ በመቃብር መፍረስ መበስበስን ሊያጠፋል ወደ መቃብር ወረደ እንጂ እስከ ክርስቶስ ድረስ በነበሩ ሙታን ሲሆን እንደነበረው መፍረስ መበስበስ ያለበት በሦስተኛውም ቀን ሽቱ መቀባት የሚያስፈልገው አይደለም፡፡ አይሁድ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ካንተ ምልክት ማየት እንሻለን ባሉት ጊዜ “አመጸኛና አመንዝራ ትውልድ ምልክትን ትሻለች ከነቢዩ ከዮናስ ምልክት በቀር ሌላ ምልክት አይሰጣትም፡፡ ዮናስ በአሳአንበሪ ሆድ ውስጥ ሦስት መዓልትና ሦስት ሌሊት እንደቆየ የሰው ልጅም በምድር ሆድ ውስጥ ሦስት መዓልትና ሦስት ሌሊት ይቆያል፡፡” በማለት መቃብር እንደማያስቀረው ሙስና መቃብርን አጥፍቶ በሦስተኛው ቀን እንደሚነሣ አስቀድሞ ተናግሮ ነበር፡፡ (ማቴ.12፡39)

ወደ መቃብሩ የሄዱ ሴቶች በተደጋጋሚ በሰሙት የአይሁድ የውሸት ወሬ ምክንያት አስቀድሞ የሰሙትን የጌታ የትንሣኤውን ነገር በሙሉ እምነት መቀበል አልቻሉም ነበርና ሽቱ ለመቀባት ሄዱ፡፡ በለሊት ከወንዶቹ ቀድመውና ጨክነው ወደ መቃብሩ የሄዱበት ጥንካሬ ግን የሚደንቅ ነው፡፡ ቀድመው በመሄዳቸው ቀድመው የትንሣኤውን ብስራት ሰሙ፤ በዓይናቸውም አይተው አረጋገጡ፡፡ ጌታችን ከሙታን መካከል እንደሌለ፣ መሞቱ ሞታችንን ሊያጠፋ፣ ወደ መቃብር መውረዱም በመቃብር ፈርሶ በስብሶ መቅረትን ሊያስወግድ እንደሆነ ተረዱ፡፡

የጌታችን የሞተው ሞታችንን ለመግደል የተነሣውም እኛን ለማሥነሳት ነውና የጌታችን ትንሣኤን ስናከብር የምናከብረው ትንሣኤያችንን እንደሆነ መረዳት ያስፈልጋል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “ዘተሰቅለ በእንተ ኃጢአትነ ከመ ያጽድቀነ ወትንሥአ ከመ ያንሥአነ – ሊያጸድቀን ስለኃጢአታችን ተሰቀለ፤ ሊያነሣንም ተነሣ” ይላል፡፡ (ሮሜ.4፡25) ስለዚህ የትንሣኤን በዓል ስናከብር የተነሣንበት በዓል እያከበርን ነውና በዓሉ ሙት በሆነ ሕይወት እንዳናከብር በትንሣኤ ልቡና ተነሥተን ስለእኛ ሕይወት የተቆረሰውን የክርስቶስ ሥጋን በመብላት ደሙንም በመጠጣት ሊሆን ይገባል፡፡ በዓለ ትንሣኤ የመነሣት በዓል ነውና ለፍቅር ለአንድነት ለሰላም ከመነሣት ጋር በዓሉን ማክበር ይገባል፡፡

ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ “ወአድኃነነ በርደቱ እመስቀሉ ውስተ ሲኦል ወፈትሐ እለሀለዉ ሕየ ጻድቃነ ሙቁሐነ በኃጢአተ አዳም አቡሆሙ – ከመስቀሉ ወደ ሲኦል በመውረዱ አዳነን በዚያም በአባታቸው አዳም ኃጢአት ምክንያት የታሰሩ ጻድቃንን ፈታ፡፡ ብሎ እንዳስተማረ የምናከብረው በዓል የመፈታት በዓል ስለሆነ ከኃጢአት፣ ከክፋት ከዘረኝነትና መሰል እስራቶች ተፈትተን ልናከብረው ይገባል፡፡
በመጨረሻም በመላው ዓለም የምትገኙ ኦርቶዶክሳውያን፣ በሀገር ውስጥም ከሀገር ውጭም ያላችሁ በሰንበት ትምህርት ቤት የምታገለግሉ ወጣቶችና ሕጻናት በዓሉ ለንስኃ፣ ለአገልግሎትና ለመልካም ነገር የመነሣትና ከተለያዩ የዓለም እስራቶች የመፈታት በዓል እንዲሆንላችሁ እመኛለሁ፡፡

እንኳን ለብርሃነ ትንሣኤው አደረሳችሁ! መልካም የትንሣኤ በዓል ይሁንላችሁ!

መጋቤ ሐዲስ ጸጋ ወ/ትንሣኤ
በመ/ፓ/ጠቅላይ ቤተ ክህነት የሰ/ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሓላፊ

የሰ/ት/ቤቶች አንድነት የማኅበራዊ የትስስር ገጾችን ቤተሰብ ይሁኑ!

(የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት)

Youtube

https://www.youtube.com/@eotc-gssu

Facebook

https://www.facebook.com/gssu.eotc

Telegram

https://t.me/eotcgssu21

Tiktok

@eotc_gssu

፵፫ኛው የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ተጀመረ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን በየዓመቱ የሚደረገው የመንበረ ፖትርያርክ የጠቅላይ ቤተክህነት ፵፫ኛው የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤበዛሬው ዕለት ተጀመረ። በመክፈቻው ጉባኤ የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያት ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት “እንደ ዐስራ ኹለቱ ሐዋርያት መንጋውን ትጠብቁት ዘንድ መንገዱን አሳምሩ” በሚለው በቅዱስ ያሬድ ቃል ተነስተው በሁለት ጉዳዮች ላይ ያተኮረ መልዕክትን አስተላልፈዋል።

የመጀመርያው መልዕክታቸው አስተዳደራዊ ጉዳዮች ላይ ያተኮረ ሲሆን “በዚህ ዘመን በሐዋርያት መንበር ላይ ለመንጋውና ለመንግሥተ እግዚአብሔር የተሾምን እንደመሆናችን በመልካም አስተዳደርና በቀና እምነት ልናስተዳድር ይገባል። በአሁን ሰዓት የቤተክርስቲያን አስተዳደር ችግር በብዛት የሚስተዋልበት እንደመሆኑ ይህን ችግር ለመቅረፍ በጥናት ላይ በመመስረት በፍጥነት መስራት ይጠበቅብናል” ብለዋል።

ኹለተኛው መልዕክታቸውም የምዕመናንና የአገልጋዮች ሰቆቃና ሞት ላይ ያተኮረ ነው። በምዕመናንና በአገልጋዮች ላይ እስከ አሁኗ ሰዓት እያጋጠመ ያለውና ያልተቋረጠው እንግልትና ሞት እንደ ምሳሌ በምስራቅ ሸዋ ከነቤተሰቦቻቸው የተገደሉትን አባት በማንሳት እንዲህ አይነቱ ተግባር ሊቆም እንዲገባ መልዕክትን በማስተላለፍ ስብሰባው በይፋ መጀመሩን አብስረዋል።

በመቀጠል ብፁዕ አቡነ አብርሃም የጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የባሕርዳርና ምዕራብ ጎጃም ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ የሰበካ ጉባኤን ጅማሮና አሁን እስካለበት ድረስ ያለውን ታሪክ በማንሳት ይህን ሥርዓት ላበጁ አባቶች ክብርና ለዚህ ያደረሰንን አምላክ ልናመሰግን ይገባል ብለዋል። በመቀጠልም የመንበረ ፖትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት የተከናወኑ ዋና ዋና ሥራዎችን ሪፖርት አቅርበዋል።

ጉባኤውም እስከ ጥቅምት 10 የሚቀጥል ሲሆን የየሀገረ ስብከቶችን የሥራ ሪፖርትና በተለያዩ ጉዳዮች ውሳኔ ይተላለፍበታል ተብሎ ይጠበቃል።

እንደሚታረዱ በጎች ሆንን!

እንደሚታረዱ በጎች ሆንን!

እንደሚታረዱ በጎች ሆንን!

እንደሚታረዱ በጎች ሆንን!

ኢትዮጵያ አገራችን ለረጅም ዘመናት በአኩሪ ባህልና እሴት አሸብርቃ ከእኛ ደረሰች ናት። ለዚህ መልካም እሴት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሚና ጉልህ ነው። ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ግን ወርቅ ላበደረ ጠጠር እንዲሉ ቤተ ክርስቲያን የጥቃት ዒላማ ሆና ብዙ ቀስቶች ሲወረወሩባት ታያል። መንግሥትም አጥፊዎች ላይ ርምጃ ከመውሰድ ይልቅ የጥፋቱ አካልና ተባባሪ በሚመስል መልኩ በገቢርና በዝምታ አጋዥነቱን አሳይቷል። በተለይም የኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት በኦርቶዶክሳውን ላይ እየተፈጸመ ያለውን ጥቃት እንዲያስቆም ሲጠየቅ ጥቃቱን ከመካድ ጀምሮ በግልጽ አጥፊዎችን እስከ መደገፍ የደረሱ ድጋፎችን ሲያደርግ ተስተውሏል፡፡ ቁጣውና ጩኸቱ ጠንከር ሲል ጥቃቱን ለማስቆም ቃል ይገባል፤ ነገር ግን ጩኸቱ በረድ ሲል የተናገረውን ሲፈጽም አይታይም፡፡ እንዲህ መሆኑ ለገዳዮች የልብ ልብ ሰጣቸው፡፡ ቤተ ክህነቱም የክርስቲያኖች ግድያና ስቃይ ደንታ የሚሰጠው አይመስልም። በየቦታው ክርስቲያኖች ሲገደሉ ምንም ካለማለት ደረጃ የደረሰው ምን ነክቶት ነው ያሰኛል፡፡ በአርሲ ዞን የተፈጸመውን ጅምላ ጭፍጨፋ በተመለከተ ኅዳር ፳፬ ቀን ፳፻፲፮ ዓ.ም ያወጣው መግለጫም “የእንጦጦ መምህር ቢናገር በዓመት፣ ያውም እሬትን” የሚያስተርት ነው። የተሰጠው መግለጫ በሟቾቹ ከመቀለድ አይተናነስም፡፡ ችግሩን ለመንግሥትም ሆነ ለዓለም ማኅበረሰብ ለመግለጥ ካስፈለገ በሚገባ አደራጅቶ፣ ብስሉን ከጥሬ ለይቶ፣ እውነት የሆነውን ሐሰት ከሆነው አጣርቶ ነው፡፡ ይህ መግለጫ ግን ድብስብስ ያለ፣ ዓላማው የማይታወቅ ነው፡፡ ቢሆንም ግን በክርስቲያኖች ላይ እየደረሰ ያለው መከራ ማቆሚያ የሌለው፣ ለማስቆም ፍላጎት ያለው የመንግሥት አካልም የሌለ መሆኑን የሚያስገነዝብ መሆኑን መረዳት ይገባል።
በመላ ሀገሪቱ ክርስቲያኖች ተመርጠው መገደል የጀመሩት ኢሕአዴግ ደርግን አስወግዶ ሥልጣን ከያዘ ማግስት ጀምሮ መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ ለውጥ መጣ ከተባለበት ጊዜ ጀምሮ ግን ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡ በተለይም ከሐምሌ ፳፰ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም በጅግጅጋ የተጀመረው ክርስቲያኖችን መርጦ ማጥቃት በመቀጠልም በኦሮሚያ ክልል ምክንያት እየተፈለገ፣ ወፍ በበረረ፣ ዘንግ በተወረወረ ቁጥር ለመከራ ተዳርገዋል፡፡ የዓይናችሁ ቀለም አላማረንም፣ ሃይማኖታችሁን አልወደድነውም እየተባሉ በስቃይ ላይ ቢገኙም ችግሩን የሚፈታላቸው፣ ጩኸታቸውን የሚሰማቸው አልተገኘም፡፡ ይህ ብቻ ሳይሆን በአማራ ክልል ከሚሴ ዞን፣ በ፳፻፲፩ ዓ.ም ሲዳማን ራሷን የቻለች ክልል ለማድረግ መንግሥትን ጠይቀው መልስ የተነፈጋቸው የዞኑ ነውጠኞች ጥያቄውን ውድቅ ያደረጉባቸው ኦርቶዶክሳውያን የሆኑ ይመስል ከየቤታቸው እየተፈለጉ ለሞትና ለመከራ ዳረጓቸው፡፡ ሀብት ንብረታቸው ወደመ፣ ይዞታቸው እየተነጠቀ ለሌላ አካል ተሰጠ፡፡ አብያተ ክርስቲያናት ተቃጠሉ፡፡
ጥቅምት ፳፻፲፪ ዓ.ም ጅዋር መሐመድ ከመንግሥት ጋር በነበረው አለመግባባት ተከበብኩ ባለ ጊዜ ለመከራ የተዳረጉት ክርስቲያኖች ናቸው፡፡ ሰኔ ፳፻፲፪ ዓ.ም የአርቲስት ሀጫሉ ሁንዴሳን መገደል ተከትሎ በክልሉ በሚኖሩ ክርስቲያኖች ላይ መውረድ የጀመረው የመከራ ዝናብ ዛሬ ድረስ አላቋረጠም፡፡ ክርስቲያኖች በክልሉ እንዳይኖሩ በሕግ ባይከለከሉም በአመፅ እና በጉልበት ከተከለከሉ ግን ዓመታት ማለፋቸው የአደባባይ ምሥጢር ከመሆን ደረጃ ላይ ደርሷል፡፡ በተደጋጋሚ ከመንግሥት ጋር ውይይት ተደርጎ ችግሩን እንፈታዋለን እየተባለ ቃል ቢገባም ችግሩ እየባሰበት እንጂ እየተሻለ አለመምጣቱ ቤተ ክርስቲያን የሐዘን መግለጫ ከማውጣት ያለፈ ተግባር መፈጸም እንዳለባት የሚያስገነዝብ ነው፡፡ ግን ይህ ሲሆን አይታይም።
በሰሞኑ በአርሲ ዞን የተፈጸመውን ጥቃት በተመለከተ ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ባወጣው መግለጫ “በሶሌ ዲገሉ እና ጢጆ ለቡ በተባሉ ቀበሌዎች ፳፰ ኦርቶዶክሳዊያን ከየቤታቸው ተለቅመው የተገደሉ ሲሆን ከእነዚህ ውስጥም ፯ቱ ሴቶችና ፳፩ ወንዶች መሆናቸው ታውቋል። በዚህ ጥቃትም እድሜያቸው ከሰባ ዓመት አዛውንት እስከ ሃያ ስምንት ቀን ጨቅላ ሕጻናት ይገኙበታል። በተመሳሳይ በዲገሉ ማርያም ቤተ ክርስቲያን ፭ ኦርቶዶክሳዊያን ከመገደላቸው በተጨማሪ የሦስት ኦርቶዶክሳውያን ቤት ደግሞ ሙሉ በሙሉ ተቃጥሏል። ከዚህ ቀደም በሮቤ አንዲቶ ደብረ ምጥማቅ ማርያም ቤተ ክርስቲያን በዓለ ማርያምን አክብረው ወደ ቤታቸው በመመለስ ላይ የነበሩ ሦስት ኦርቶዶክሳዊያን ጨለማን ተገን ባደረጉ ነፍሰ ገዳዮች መገደላቸው ይታወሳል። የሀገረ ስብከቱ የሥራ ኃላፊዎች ከመንግሥት የጸጥታ አካላት ጋር በተደጋጋሚና ሆን ተብሎ በሚፈጸመው የኦርቶዶክሳዊያን ጥቃት ዙሪያ በጋራ እየሠሩ የሚገኙ ሲሆን በዚህ ዐይነት የጥቃት ተግባር ላይ ተሰማርተው የሚገኙ አንዳንድ አካላት ላይ በመንግሥት በኩል የማያዳግም ርምጃ እንደተወሰደባቸው ሀገረ ስብከቱ በላከው ሪፖርት አረጋግጠዋል” በማለት ዘርዝሮታል።
ቢቢሲ አማርኛ የደረሰውን ጥቃት የዘገበው “በጥቃቱ የቤተሰብ አባላት የተገደሉባቸው በሽርካ ወረዳ፣ የጥዮ ለቡ ቀበሌ ነዋሪ፣ ኅዳር ፲፫ ቀን ፳፻፲፮ ዓ.ም. ግድያው ሲፈጸም በአጋጣሚ በስፍራው ባለመኖራቸው እርሳቸው ቢተርፉም፣ አብዛኞቹ የቤተሰቦቻቸው አባላት እንደተገደሉባቸው ተናግረዋል። በጥቃቱ ባለቤቴ እና ልጄ፣ የአባቴ ልጆች፣ የአባቴ ሚስት፣ እኅቶቼ እና ወንድሞቼ በአጠቃላይ ሰባት ቤተሰብ ተገድለውብኛል። ከቤት ወስደው ነው የጨፈጨፏቸው” ብለዋል በመሪር ሐዘን። ቢቢሲ ባነጋገራቸው ወቅትም ከጥቃቱ የተረፉ የሁለት ዓመት እና የስምንት ዓመት ልጆቻቸውን አሳክመው እየተመለሱ እንደ ሆነ ተስፋ በቆረጠ ሁኔታ ገልጸዋል። በወረዳው ሾሌ ዲገሊቡና ቀበሌ ነዋሪ የሆኑ ሌላ ግለሰብም ባለፈው ሳምንት በተፈጸመው ጥቃት የስምንት ልጆቻው እናት የሆነችው ባለቤታቸው እና የ፲፪ ዓመት ሴት ልጃቸው እንደተገደሉባቸው ለቢቢሲ ተናግረዋል” በማለት ነው።
ከሳምንት በፊት በደራ ወረዳ በክርስቲያኖች ላይ የተፈጸመው ግድያ በልዩ ልዩ ብዙኀን መገናኛ ተዘግቦ አይተናል ሰምተናልም፡፡ እነዚህ ክርስቲያኖች በሰማዕትነት እንዲጠሩ የአምላካችን ፈቃድ ቢሆንም ከክርስቲያኖች የሚጠበቅ ተግባርና ሐላፊነት መኖሩን መዘንጋት አይገባም፡፡ እንዲህ ያለው አሰቃቂ ግድያ ሲፈጸም ጥቃቱን እንዲያስቆም መንግሥትን ከመጠየቅ ጀምሮ ሌሎች ተግባራትን ማከናወንም ይገባል፡፡ ዝም አላችሁ ላለመባል ብቻ ለግብር ይውጣ የሚሰጡ መግለጫዎች ግን ክርስቲያኖችን ተስፋ ያስቆርጣሉ፡፡ ከዚህ በተጨማሪም በአባቶች ላይ ያለው አመኔታ እንዲቀንስ ስለሚያደርግ ሊታሰብበት ይገባል፡፡ መንግሥትም ዜጎቹን ነቅቶና ተግቶ የመጠበቅ ሐላፊነቱን መወጣት ይኖርበታል፡፡

ይህ ዐይነቱ ኦርቶዶክሳውያን ላይ ያነጣጠረ ግድያ እንዲቆምና የወንጀሉ ፈጻሚዎችም ለፍርድ እንዲቀርቡ በሀገረ ስብከቱ በኩል እየተደረገ ያለው ጥረት እንደተጠበቀ ሆኖ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጠቅላይ ጽሕፈት ቤትም በድርጊቱ እጅጉን ማዘኑን እየገለጸ ጉዳዩን ከሚመለከታቸው የመንግሥት አካላት ጋር በመሆን የሚከታተለው መሆኑን ለመግለጽ እንወዳለን። በሌሎች ስፍራዎች የሚያጋጥሙ ተመሳሳይ ጥቃቶችን በእንጭጩ ለመቅጨትና ከሚመለከታቸው የመንግሥት አካላት ጋር በመነጋገር መፍትሔ ማበጀት ይቻል ዘንድ አህጉረ ስብከት ችግሮች በሚያጋጥሙ ወቅት ሪፖርት እንዲልኩ ቀደም ሲል በደብዳቤ በተላከላቸው የስልክና ዘመናዊ የመገናኛ ዘዴዎች አማካኝነት በፍጥነት በማሳወቅ ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ እያሳሰብንና ለሞቱት ኦርቶዶክሳውያን ወገኖቻችን ሁሉ ልዑል እግዚአብሔር መንግሥተ ሰማያትን እንዲያወርስልን በመጸለይ የፌዴራልም ሆነ የክልል መንግሥታት የሚደርሱ ሃይማኖት ተኮር ጥቃቶች እንዲቆሙና መሰል ጥቃት እንዳይፈጸም ለኦርቶዶክሳዊያን ወገኖቻችን ከለላ እንዲሰጡልን እንጠይቃለን̋ ተብሎ የተነገረውን አጠናክሮ መቀጠል እንጂ በቃል እየተናገሩ ከተግባሩ መራቅ ብዙ ዋጋ ያስከፍላል።

ባይተዋርነት እስከ መቼ? ክፍል ሁለት

ባይተዋርነት እስከ መቼ? ክፍል ሁለት

ባይተዋርነት እስከ መቼ? ክፍል ሁለት

ባይተዋርነት እስከ መቼ? ክፍል ሁለት

በክፍል አንድ ጽሑፋችን ኦርቶዶክሳውያን በሀገራችን ባይተዋር ያደረጉንን ጥቂት ምክንያቶች ለማየት ሞክረናል፡፡ በዛሬው ጽሑፋችን ደግሞ ከዚህ ባይተዋርነት የመውጫ መንገዶችን ለመጠቆም እንሞክራን፡፡
1. ለሰማያዊ ክብር፣ ለዘላለማዊ ሕይወት የሚያበቃ መንፈሳዊ ዝግጅት ይኑረን፡- እንደ ቃሉ የምንኖር እምነተ ብርቱዎች እና ከምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን በአግባቡ የምንካፈል መሆን አለብን፡፡ ይህ መንፈሳዊ ዝግጅት እንደ ጥንቶቹ ጽኑ ክርስቲያኖች በአሕዛብ ፊት ያለ ፍርሃት “እኛ የተሰቀለውን ክርስቶስን እንሰብካለን” የምንል የዐደባባይ ምስክሮቹ እንድንሆን ያበረታናል፡፡ “ልንሔድ ከክርስቶስ ጋር ልንኖር እንናፍቃለን” ለማለት ያበቃናል፡፡ በቤተ ክርስቲያን ላይ የሚፈጸመውን በደል ለመቃወም እና ፍትሕ ርትዕ ለመጠየቅ ብሎም ለማስፈን እንድንችል፣ የፍርሃትን መንፈስ ገድለን የኃይልና የሥልጣንን መንፈስ እንድንለብስ ያደርገናል፡፡ Read more

በረሃብ ከመሞት በጦርነት መሞት ይሻላል

በረሃብ ከመሞት በጦርነት መሞት ይሻላል

በረሃብ ከመሞት በጦርነት መሞት ይሻላል

በረሃብ ከመሞት በጦርነት መሞት ይሻላል

ዓለም ለዘመናት የተለያዩ መከራዎችንና ፈተናዎችን አስተናግዳለች። የብዙዎቹ ችግሮች ምንጮች ደግሞ ሰው ሠራሽ ናቸው። ሰው በእግዚአብሔር አርአያ መፈጠሩ፣ ዐዋቂና አስተዋይ ፍጡር መሆኑ ለችግሮቹ መፍቻ ቁልፍ ለማግኘት እንዲችል አድርጎታል። በዚያው ልክ ራሱ ለፈጠራቸው ችግሮች መፍትሔ አጥቶ ሲባዝን ይታያል። በዚህም ምክንያት ሰው የስኬቱ ተጎጂ (the victim of his own success) ሆኗል። Read more

የሰላም ዋጋው ስንት ነው?

የሰላም ዋጋው ስንት ነው?

የሰላም ዋጋው ስንት ነው?

የሰላም ዋጋው ስንት ነው?

ሰላም የሚለው ቃል ሲጠራ ቀላል ቢመስልም ዋጋው ግን በገንዘብ ከመተመን በላይ ነው፡፡ ሰላም እንኳን ለሰው ልጅ ለእንስሳት፣ ለአራዊት እና በጠቅላላው ለሥነ ፍጥረት በጣም አስፈላጊ ነገር ነው፡፡ ሰላም ከሌለ ማንም ወጥቶ መግባት፣ ነግዶ ማትረፍ፣ አርሶ መብላት፣ ደግሶ መዳር አይችልም፡፡ ሠርቶ የመለወጥን ተስፋም ያመነምናል፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በጸሎተ ቅዳሴዋ “እግዚአብሔር በይቅርታው አንድ ያደርገን ዘንድ ስለ ሰላም እንማልዳለን፤ በዘመኑ ሁሉ ፍጹም ሰላምን እግዚአብሔር ይሰጣት ዘንድ እግዚአብሔርን ስለምትወድ ስለ አገራችን ኢትዮጵያ እንማልዳለን” በማለት ዕለት ዕለት ፈጣሪዋን የምታሳስበው ያለ ምክንያት አይደለም – ሰላም የሁሉ ነገር መሠረት ስለሆነ እንጂ፡፡ እንኳን ሰማያዊ ለሆነው ሃይማኖት ለምድራዊ ኑሮም ቢሆን ዓለም የምትሸልመው ሳይታክቱ ለሰላም የደከሙትን ነው፡፡ Read more

ባይተዋርነት እስከ መቼ?

ባይተዋርነት እስከ መቼ?

ባይተዋርነት እስከ መቼ?

ባይተዋርነት እስከ መቼ?

 መስከረም ፲፭ ቀን ፳፻፲፮ ዓ.ም. በአርሲ ሀገረ ስብከት በሆንቆሎ ዋቤ ወረዳ ቤተ ክህነት ኦርቶዶክሳውያን ተገደሉ (ሰባት ኦርቶዶክሳውያን)፡፡ ኦርቶዶክሳውያን ጨቅላ ሕፃናትን ጨምሮ የካህናት ቤተሰብ በአሰቃቂ ሁኔታ በጥይት ተደብድበው ተገደሉ፡፡ በርካቶች ቆሰሉ፡፡
 ካህናት እና ቤተሰቦቻቸው ከቤተ ክርስቲያን እስከ ቤታቸው ታድነው ይገደላሉ፡፡
 መስከረም ፳፫ ቀን ፳፻፲፮ ዓ.ም.) በምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት በአዳማ ዙሪያ ወረዳ ቤተ ክህነት በአርቱ መካነ ቅዱሳን ቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች የሆኑት አባ ተክለ አብ እና ቀሲስ መሠረት ተገደሉ፡፡ በደራ፣ በወለጋ፣ በቤንሻንጉል ወዘተ
 አሮጌው ዓመት(፳፻፲፭ ዓ.ም.) በስልጤ ዞን የተለመደውን የኦርቶዶክሳውያን ደም በማፍሰስ፣ ሀብት ንብረታቸውን በማቃጠል እና በማሳደድ ነው የተሰናበተን፡፡ አዲሱ ዓመት ደግሞ የአሮጌውን ዓመት የደም ግብር መገበርን አጠናክሮ ቀጥሎበታል፡፡
 ካህኑ በዐውደ ምሕረት በአገልግሎት ላይ እያሉ በጥይት የተመቱት ጠረፍ አካባቢ በምትገኘው አጥቢያ አይደለም፡፡ እዚሁ አዲስ አበባ ነው፡፡ Read more

ክርስትና ከዘውግ ባሻገር የሆነ ማንነት

ክርስትና ከዘውግ ባሻገር የሆነ ማንነት

ክርስትና ከዘውግ ባሻገር የሆነ ማንነት

ክርስትና ከዘውግ ባሻገር የሆነ ማንነት

የሰው ልጅ ሁሉ ከአዳም የተገኘ የእግዚአብሔር አምላክ የእጅ ሥራ ነውና ከላይ በቀለም በቅርፅ ወዘተ ልዩነት ቢኖረው እንኳ የሚመሳሰልበት ከውስጥ የሆነ ሥነ-ሕይወታዊ አንድነት አለው፡፡ ይህም ተመሳሳይ ተፈጥሮአዊ እና ሥነ ልቡናዊ (Bio-Psychic Union) ውቁር እንዲኖረው አድርጓል፡፡ በማኅበራዊ ፍጡርነቱ በፈጠረው በማኅበራዊ መስተጋብሩ ምክንያት ደግሞ በሒደት ራሱን ካንድ የባህል መሠረት ካለው ማንነት ጋር ያዛምዳል፡፡ ይህ ልዩነት ደግሞ የተለያየ አስተሳሰብ/ እና የአረዳድ አድማስ እንዲኖረው ያደርገዋል፡፡ ክርስትና ለነፍሳችን መድኅን የሆነው የእውነትና የሕይወት መንገድ ጌታችን መድኃኒታችን ክርስቶስ ኢየሱስ ብቻ መሆኑን ያስተምራል፡፡ ክርስቲያንም ይህን እውነት ብቻ ይከተላል፡፡ ከአምልኮ መልስ ባለው ማኅበራዊ መስተጋብር ግን ብዝኃነትን ያከብራል፡፡ Read more