ወቅታዊ መልእክት

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ (ሀገር አቀፍ) የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ከውጪና ከውስጥ የሚቃጡባትን ፈተናዎች በመቋቋም ከውጭ የሚቃጡባትን ፈተናዎች ሰማዕትነትን በሚቀበሉ ልጆቿ ምስክርነት፣ ምንፍቅናን በቃል የመጣውን በቃል በመጻሕፍት የመጣውን በመጻሕፍት በመመከት ሐዋርያዊ ቅብሎሿን ጠብቃ መሠረተ እምነቷን፣ ዶግማና ቀኖናዋን ቅዱስ ትውፊቷን ለትውልዱ እያስተማረች ጸንታ ቆይታለች፤ ወደ ፊትም ትኖራለች፡፡

ቤተ ክርስቲያናችን ዛሬ በልዩ ልዩ ውጫዊ ፈተናዎች ዋጋ እየከፈለች ያለች ቢሆንም ከሁሉ የከፋው ግን ከክብር በላይ የላቀ ክብር ባጎናጸፈቻቸውና እረኛና ጠባቂ እንዲሆኑ ባሰማራቻቸው ልጆቿ በተደጋጋሚ እየገጠማት ያለው የቀኖና ጥሰት ነው። የጥር ፲፬ ጳጳሳት ሹመት፣ የትግራይ ሲኖዶስ፣ የቅባት ጳጳሳት ሹመት ፤ ፖለቲካን ተጠግቶ ቤተክርስቲያንን የማጥቃት ክፉ ግብር ሳያንሳት ፤በተገኘው አጋጣሚ ኹሉ የምንፍቅና ትምህርቶች የሚያስተላፉትን በዝምታ መመልከት እየበዛና በዚህም በጎቿን ከበረቷ ለማስነጠቅ ለሚሠሩ ሁሉ ተባባሪ በመሆን የሚኬድበት ርቀት ቤተክርስቲያኒቱን ዋጋ እያስከፈለ በመሆኑ በቃ ሊባል ይገባዋል፡፡ ለማሳያ ይሆን ዘንድ በአቡነ በርናባስ መባልእትንና ነገረ ክርስቶስን አስመልክቶ፤ በአቡነ ፊልጶስ እመቤታችንና ሥላሴን አስመልክቶ የተናገሩትን የስሕተት ትምህርቶች ቅዱስ ሲኖዶስም ሆነ የሊቃውንት ጉባኤ በወቅቱ ማስጠንቀቂያም ሆነ የእርምት እርምጃ ባለመውሰዳቸው ዛሬ በአቡነ ገብርኤል እመቤታችንንና ነገረ ክርስቶስን አስመልክቶ ያውም በዐውደ ምሕረት፣ እንዲሁም በዕለተ ስቅለት በተደረገ የአዳራሽ ጉባኤ ለተናገሩት የኑፋቄ ትምህርት አድርሶናል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ቤተ ክርስቲያን ገፊ እንደሆነች እና ስለክርስቶስ የሚዘምሩትን እንደምታባርር እርሷም ስለ ክርስቶስ እንደማትዘምር በአደባባይ በጉባኤ ያለምንም ፍርሀት ሲናገሩ ተደምጠዋል፡፡

ከዚህም ባለፈ የማኅበራት ምዝገባ ክትትልና ቁጥጥር መምሪያን ጨምሮ የተለያዩ ሊቃነ ጳጳሳት በኑፋቄ ትምህርት ማስፋፋት ላይ የተሰማራውን “ፍኖተ ጽድቅ” ማኅበርን በገንዘቡ በሚሠራቸው የስቱዲዮ ግንባታ፣ የመጽሐፍ ኅትመት እና የመሳሰሉት ተግባራት በመማረክ የቤተክርስቲያንን ክብር አሳልፈው ሰጥተዋል፡፡ በዚህ ሂደት ላይ አንዳንድ መምህራን እና ማኅበራትም ተሳታፊ መሆናቸው በእጅጉ አሳዛኝ ነው፡፡

ይህ እንዲሆን ምክንያት ከሆኑ ነገሮች መካከል የሚከተሉት በዋናነት ተጠቃሽ ናቸው።

1. የአስተዳደር ብልሹነት የወለደው ዘርፈ ብዙ ችግር
በእኛ መረዳት አሁናዊው ፈተና እና ችግር ከውጪያዊው የዝግጅት ጥቃትና ፈተናም በላይ የበረታው የውስጥ ችግር ነው። ለዚህም ዋናውና አንደኛው የሁለንተናዊ ድካማችን ምክንያት የቤተ ክህነቱ ብልሹ አስተዳደር ነው።
አሁን ላይ ያለው የቤተ ክህነት አስተዳደር ዘመኑን በመዋጀት የቤተ ክርስቲያንን መንፈሳዊ ተልዕኮ በማስፈፀም ነፍሳትን ለመንግሥተ እግዚአብሔር ለማብቃት የሚያስችል ቁመና እና ብቃት ላይ አይገኝም ። ሕግ አውጪ፣ ሕግ ፈፃሚ እና ሕግ ተርጓሚ አንድ አካል በመሆን፣ ተጠቅልሎ በተያዘ ሥልጣን ቤተ ክርስቲያኒቱ እጅ ተወርች ተቀፍድዳ ወደ ትውልዱ እንዳትደርስ እየተሠራ ይመስላል።

ቤተ ክርስቲያን በማይመጥናት ደካማ አስተዳደር ምክንያት ከተመሠረተችበት ነፍስ የማዳን መንፈሳዊ ተግባር ተናጥባለች። አስተዳደሩ ምእመናንን ለመንፈሳዊ ፍሬ ከማብቃት ይልቅ ለውድቀታቸው ምክንያት ሆኗል። በተለያዩ ጊዜያት ተጠንተው የቀረቡ ልዩ ልዩ የአስተዳደር ማሻሻያዎች እየተኮላሹ ጉዞው ከድጡ ወደ ማጡ ሆኗል:: በ ፳፻ወ፬ ዓ.ም ለሲኖዶስ የቀረበው የመሪ ዕቅድ ትግበራ ጥያቄ ፲፫ ዓመታት ሲገፋ ቆይቶ አሁንም ቦታ ተነፍጐታል። አስተዳደራዊ ለውጥ ጠልነቱ ተባብሶ ቀጥሏል። እኔ ብቻ በሚሉ ፣ ቤተ ክርስቲያን እንደ ግል ተቋማቸው በሚያዩ አካላት ተወራለች:: በሃይማኖት ችግር ፣ በቀኖና ጥሰት እና በሙስና ተጠያቂ መሆን የሚገባቸው አካላት የተሻለ ሹመትና ሽልማት ይሰጣቸዋል፡፡

2. ለሊቃውንት ጉባኤ ትኩረት መነፈጉ
የሊቃውንት ጉባኤ ተገቢው ትኩረት ሳይሰጠው በመቅረቱ ፣ እንዲሁም ሊቃውንት ክብራቸው ባለመጠበቁ እና ከውሳኔ ሰጪነት ድርሻ በመገለላቸው ፤ ለስሑት ትምህርት በሚገባው መልኩ ምላሽ መስጠት የማይችል ሆኗል:: እንዲሁም በቤተክርስቲያኒቱ ስም ለሚታተሙና ለሚሰራጩ መጻሕፍትና ልዩ ልዩ የምስልና የድምፅ እንዲሁም የኅትመት ውጤቶች የመገምገምና ዕውቅና የመስጠት ሥልጣኑ ተነጥቋል። የአደረጃጀትና የመከላከል አቅሙ በመዳከሙ፤ በመዋቅሩ ውስጥ የተሰገሰጉ ሐሰተኛ መምህራን በአፍም በመጽሐፍም ስሁት ትምህርታቸውን በቤተ ክርስቲያኒቱ ዐውደ ምሕረት እያሰራጩ ይገኛሉ።

ትናንት አባቶች ያቆዩትን ሀብት መንዝሮ መጠቀም እንጂ የራሳቸውን አሻራ የማያኖሩ፣ ሀብት ንብረቷን ጠብቀው ከማቆየት ይልቅ ለግል መዝብረው ቀሪውን ለዘራፊ አሳልፈው የሰጡ ከመንፈሳዊ ክብር በጐደሉ፣ በሥጋ ሐሳብ ጨርሶውኑ በተወሰዱ፣ ምግባር በጎደላቸው ከአጥቢያ ጀምሮ እስከ ሊቃነ ጳጳሳት ድረስ ባሉ አገልጋዮች እየተፈተነች ትገኛለች።
ያለ ዋጋ ከሚሰጠው መንፈሳዊ ሹመት ጀምሮ የቤተ ክርስቲያንን መንፈሳዊ አገልግሎት የሚጎዳ እኩይ ተግባር በእጅ መንሻ የሚፈጽሙ አካላት በሁሉም መዋቅር ውስጥ ተሰግስገው ቤተ ክርስቲያን የተመሠረተችበትን ዓላማ እንዳታሳካ ሳንካ ሆነውባታል።

ስንዱዋ እመቤት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በሕግ እና በሥርዓት ዝግጅቷ እንከን አይወጣላትም። ነገር ግን ከሕግና ከሥርዓት ባፈነገጡ፣ ሐሰተኛ ትምህርት በሚያሰራጩ እና ኢ-ክርስቲያናዊ በሆነ ሕይወት ወስጥ በሚመላለሱ በተለይ በሁሉም መዋቅር ወስጥ በሚገኙ አገልጋይ ሠራተኞች ላይ ተግባራዊ ርምጃ አለመወሰዱ ለምእመናን ተስፋ መቁረጥ እና ፍልሰት ምክንያት ሆኗል።

3. በሕግ ከተሰጣቸው መብት ውጪ በማስተማር የሚሰማሩ ማኅበራትን በሕግ አግባብ ወደ መስመር አለማስገባት
የሰሞኑ ስሁት ትምህርት በሕጋዊ ዕውቅና ስም የሚንቀሳቀሱ ማኅበራት እኩይ ተግባር ከትናንት የቀጠለ የብልሹ አስተዳደር መገለጫ ነው። የማኅበራት አስተዳደር ደንብ ፀድቆ ሥራ ላይ ከመዋሉ በፊት ደንቡ ላይ የሚስተዋሉ ክፍተቶችን በማስረጃ በማስደገፍ የማሻሻያ ሐሳብ ብናቀርብም ተቀባይነት ሳያገኝ ቀርቷል። በመሆኑም የፈራነው ደርሶ ፤ ደንቡን ለማስፈፀም የተቀመጠው የማኅበራት ምዝገባ ክትትል እና ቁጥጥር መምሪያ፤ በማኅበራት አስተዳደር ደንብ አንቀጽ ፲ ላይ የማኅበራት ዓለማ “ለትምህርት ተጠሪ ተቋማት ድጋፍ መስጠት ነው” በሚል የተደነገገ ቢሆንም እንደ ‹‹ፍኖተ ጽድቅ›› ያለ ማኅበር ድጋፍ ሰጪ ሳይሆን ፈፃሚ ሆኖ፣ ማኅበሩ ከተመሠረተበት ዓላማ ውጭ ትምህርተ ወንጌልን በአዳራሽ ውስጥ ሲሰጥ፤ በሚዲያ ትምህርት ሲያስተላልፍ አልፎ ተርፎ የቤተ ክርስቲያን መዝሙሮቿን ከሥርዓቷና ከቀኖናዋ ውጪ በሆነ ሁኔታ በሚዲያ እያቀናበረ ሲያስተላልፍ ተገቢው አስተዳደራዊም ሆነ ቀኖናዊ እርምጃ እንዲወሰድ ከማድረግ ይልቅ በማኅበርነት በመመዝገብ እንዲሁም በደንቡ የተሰጠውን የመቆጣጠር ሓላፊነት የማኅበራት ማደራጃ ምዝገባ ክትትል እና ቁጥጥር መምሪያ ባለመወጣቱ ዛሬ ለደረሰው ስሑት ትምህርት ዝግጅትና ስርጭት አብቅቶናል፡፡
ይኽ ማኅበር ከኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አስተህምሮ ውጪ ስሑት ትምህርት የሚሰጥበት ተቋም እንደሆነ በተጨባጭ እየታወቀ እና በአካል ቀርበው አረጋግጠው እንኳን ቅዱስ ፓትርያርኩን በዚያ ሥፍራ እንዲገኙ በማድረግ ቤተ ክርስቲያንን አሳልፈው የሰጡ የቤተክርስቲያኒቱ አገልጋዮች መኖራቸው የአደባባይ ሐቅ ነው፡፡

በመሆኑም ከዚህ በታች የዘረዘርናቸው ትኩረት የሚሹ ጉዳዮች ተገቢው ትኩረት እንደሚሰጣቸው እና የእርምት እርምጃ እንደሚወሰድባቸው እናምናለን።

1. የሊቀ ጳጳሱ ኢ-ኦርቶዶክሳዊ አስተምህሮ በቅዱስ ሲኖዶስ ቀኖናዊ እርምጃ እንደሚወሰድበት ብናምንም በሚገባ እና በትኩረት ጉዳዩ እንዲታይና መፍትሔ እንዲሰጠው፡፡ እንዲሁም በተመሳሳይም ስሑት ትምህርቶችን የሚያስተምሩ እና ያስተማሩ ሌሎች ጳጳሳት እና መምህራን ጉዳይም አብሮ እንዲታይ፣ ይኽን አጋጣሚ ተጠቅሞ የሊቃውንት ጉባኤም በስሑት አስተምህሮዎች ላይ ተገቢውን ምላሽ እንዲሰጥ ቢደረግ፡፡

2. ሓላፊነቱን በአግባቡ ያልተወጣው የማኅበራት ምዝገባና ክትትል እና ቁጥጥር መምሪያ ከሊቀ ጳጳሱ ጀምሮ በየደረጃው ያሉ ሓላፊዎች እንዲጠየቁ፡፡

3. የማኅበራት ምዝገባ ክትትልና ቁጥጥር መምሪያ የዕውቅና ሰርተፊኬት ከመቸርቸር ወጥቶ፣ ደንቡና አሠራሩን ዳግመኛ በመፈተሽ፣ የዕውቅና አመዘጋገብ፣ ክትትልና ቁጥጥር ሒደቱም ንጥር ያለ እና መስፈርቶች የወጡለት እንዲሆን፡፡

4. ቅዱስ ፓትርያርኩን በማሳሳት ” ፍኖተ ጽድቅ ” በተባለው ማኅበር ዝግጅት ላይ እንዲገኙ ያደረጉ የቅዱስ ፓትርያርኩ ልዩ ጽ/ቤት ሓላፊና የፖትርያርኩ የፕሮቶኰል ሹም እንዲጠየቁ፡፡

5. ‹‹ፍኖተ ጽድቅ›› የተሰኘው ማኅበር በቤተክርስቲያን ላይ እያደረሰ ያለውን የተሐድሶ ኑፋቄ ትምህርት ባለማረሙ ምክንያት ማኅበሩ የምዝገባ ፈቃዱ ተሰርዞ ባስተላለፈው ትምህርቶች በቀኖና እንዲጠየቅ እና በዚሁ አጋጣሚ ከመምህራን እስከ ሊቃነ ጳጳሳት “ፍኖተ ጽድቅ” ከተባለ ማኅበር ጋር የጀመሩት በነዋይ ላይ የተመሠረተ ግንኙነት በአስቸኳይ እንዲቆም እንዲደረግ። እንዲሁም በቤተ ክህነቱ የበላይ ሓላፊዎች በኩል እናት ቤተ ክርስቲያናችን አንዳች ሳይጎድልባት ባልተገባ መሻት ከባለ ጸጋ እጅ ለማኝ በማድረግ ቅድስት ቤተክርስቲያንን የማዋረድ እና አሳልፎ የመስጠት እኩይ ተግባር እንዲቆም።

6. የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት ኦርቶዶክሳዊት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊ አገልግሎቷን እንዳታሰፋ እጅ ተወርች ቀፍድዶ የያዛት ደካማ፣ ብልሹ አስተዳደር እንዲስተካከል በልጅነት መንፈስ በተደጋጋሚ የችግሮቹን ማሳያና መፍትሔዎቹን፣ ሥርዓተ መዋቅርን በመጠበቅ እስከ ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ድረስ ቢያቀርብም ተጨበጭ ምላሽ አልተሰጠውም ። ይህም ጉዳይ ከግንዛቤ ገብቶ አፋጣኝ መፍትሔ ሊሰጠው ይገባል።

ነገር ግን አሁንም እንደ ቀድሞው ተሸፋፍኖ የሚታለፍ እና መፍትሔ ከመስጠት ይልቅ ታላቋን ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስትያን የማይመጥነው ብልሹ አስተዳደር የሚቀጥል ከሆነ በዓለም አቀፍ ደረጃ ከሚገኙ ሊቃውንት፣ ምእመናን፣ እና የሰንበት ት/ቤት አባላት ጋር በመሆን የምንረከባትን እና ለትውልድ የምናሰረክባትን እናት ቤተ ክርስቲያን የምንታደግበትን መንገድ የምንከተል መሆኑን በዚሁ አጋጣሚ ለመግለፅ እንወዳለን።

የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት
ሚያዚያ ፳፩ቀን ፳፻፲ወ፯ ዓ.ም
አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ

የሰ/ት/ቤቶች አንድነት የማኅበራዊ የትስስር ገጾችን ቤተሰብ ይሁኑ!

(የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት)

Youtube

https://www.youtube.com/@eotc-gssu

Facebook

https://www.facebook.com/gssu.eotc

Telegram

https://t.me/eotcgssu21

Tiktok

@eotc_gssu

“ኢሀሎ ዝየ ዳእሙ ተንሥአ በከመ ይቤ – ከዚህ የለም እንደ ተናገረው ተነሥቷል፡፡” ማቴ.28፡6

በጌታችን በመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መቃብር በራስጌና በግርጌ የነበሩ ቅዱሳን መላእክት ማልደው ወደ ጌታ መቃብር ለሄዱ ሴቶች ሕያውን ከሙታን መካከል ስለምን ትፈልጋላችሁ ከዚህ የለም እንደ ተናገረው ተነሥቷል በማለት መልሰውላቸዋል፡፡ ሴቶቹ ወደ መቃብሩ መሄድ የጌታችንን ሥጋ ሽቱ ለመቀባት ነበር፡፡ ነገር ግን እንደ ጠበቁት ሦስት ቀን የሞላው ጠረኑ የተቀየረ ሥጋ ሳይሆን ባዶ መቃብር ነበር ያገኙት፡፡ ማስተዋል አቅቷቸው እንጂ ጌታችን ከሞቱ አስቀድሞ “ይህንን ቤተ መቅደስ አፍርሱት በሦስተኛው ቀን አነሣዋለሁ” ብሎ በሥልጣኑ በሦስተኛው ቀን እንደሚነሣ ነግሯቸው ነበር፡፡ (ዮሐ.2፡18) በሌላም የወንጌል ክፍል “ያለ እኔ ፈቃድ ነፍሴን ከሥጋዬ የሚለያት የለም፤ እኔ ወድጄ እለያታለሁ እንጂ በመቃብር ላኖራት አዋሕጄም ላስነሣት ሥልጣን አለኝ፡፡” በማለት ስለሞቱና ስለ ትንሣኤው ተናግሮ ነበር፡፡ (ዮሐ.10፡18)

የጌታችን ሥጋ በመቃብር መፍረስ መበስበስን ሊያጠፋል ወደ መቃብር ወረደ እንጂ እስከ ክርስቶስ ድረስ በነበሩ ሙታን ሲሆን እንደነበረው መፍረስ መበስበስ ያለበት በሦስተኛውም ቀን ሽቱ መቀባት የሚያስፈልገው አይደለም፡፡ አይሁድ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ካንተ ምልክት ማየት እንሻለን ባሉት ጊዜ “አመጸኛና አመንዝራ ትውልድ ምልክትን ትሻለች ከነቢዩ ከዮናስ ምልክት በቀር ሌላ ምልክት አይሰጣትም፡፡ ዮናስ በአሳአንበሪ ሆድ ውስጥ ሦስት መዓልትና ሦስት ሌሊት እንደቆየ የሰው ልጅም በምድር ሆድ ውስጥ ሦስት መዓልትና ሦስት ሌሊት ይቆያል፡፡” በማለት መቃብር እንደማያስቀረው ሙስና መቃብርን አጥፍቶ በሦስተኛው ቀን እንደሚነሣ አስቀድሞ ተናግሮ ነበር፡፡ (ማቴ.12፡39)

ወደ መቃብሩ የሄዱ ሴቶች በተደጋጋሚ በሰሙት የአይሁድ የውሸት ወሬ ምክንያት አስቀድሞ የሰሙትን የጌታ የትንሣኤውን ነገር በሙሉ እምነት መቀበል አልቻሉም ነበርና ሽቱ ለመቀባት ሄዱ፡፡ በለሊት ከወንዶቹ ቀድመውና ጨክነው ወደ መቃብሩ የሄዱበት ጥንካሬ ግን የሚደንቅ ነው፡፡ ቀድመው በመሄዳቸው ቀድመው የትንሣኤውን ብስራት ሰሙ፤ በዓይናቸውም አይተው አረጋገጡ፡፡ ጌታችን ከሙታን መካከል እንደሌለ፣ መሞቱ ሞታችንን ሊያጠፋ፣ ወደ መቃብር መውረዱም በመቃብር ፈርሶ በስብሶ መቅረትን ሊያስወግድ እንደሆነ ተረዱ፡፡

የጌታችን የሞተው ሞታችንን ለመግደል የተነሣውም እኛን ለማሥነሳት ነውና የጌታችን ትንሣኤን ስናከብር የምናከብረው ትንሣኤያችንን እንደሆነ መረዳት ያስፈልጋል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “ዘተሰቅለ በእንተ ኃጢአትነ ከመ ያጽድቀነ ወትንሥአ ከመ ያንሥአነ – ሊያጸድቀን ስለኃጢአታችን ተሰቀለ፤ ሊያነሣንም ተነሣ” ይላል፡፡ (ሮሜ.4፡25) ስለዚህ የትንሣኤን በዓል ስናከብር የተነሣንበት በዓል እያከበርን ነውና በዓሉ ሙት በሆነ ሕይወት እንዳናከብር በትንሣኤ ልቡና ተነሥተን ስለእኛ ሕይወት የተቆረሰውን የክርስቶስ ሥጋን በመብላት ደሙንም በመጠጣት ሊሆን ይገባል፡፡ በዓለ ትንሣኤ የመነሣት በዓል ነውና ለፍቅር ለአንድነት ለሰላም ከመነሣት ጋር በዓሉን ማክበር ይገባል፡፡

ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ “ወአድኃነነ በርደቱ እመስቀሉ ውስተ ሲኦል ወፈትሐ እለሀለዉ ሕየ ጻድቃነ ሙቁሐነ በኃጢአተ አዳም አቡሆሙ – ከመስቀሉ ወደ ሲኦል በመውረዱ አዳነን በዚያም በአባታቸው አዳም ኃጢአት ምክንያት የታሰሩ ጻድቃንን ፈታ፡፡ ብሎ እንዳስተማረ የምናከብረው በዓል የመፈታት በዓል ስለሆነ ከኃጢአት፣ ከክፋት ከዘረኝነትና መሰል እስራቶች ተፈትተን ልናከብረው ይገባል፡፡
በመጨረሻም በመላው ዓለም የምትገኙ ኦርቶዶክሳውያን፣ በሀገር ውስጥም ከሀገር ውጭም ያላችሁ በሰንበት ትምህርት ቤት የምታገለግሉ ወጣቶችና ሕጻናት በዓሉ ለንስኃ፣ ለአገልግሎትና ለመልካም ነገር የመነሣትና ከተለያዩ የዓለም እስራቶች የመፈታት በዓል እንዲሆንላችሁ እመኛለሁ፡፡

እንኳን ለብርሃነ ትንሣኤው አደረሳችሁ! መልካም የትንሣኤ በዓል ይሁንላችሁ!

መጋቤ ሐዲስ ጸጋ ወ/ትንሣኤ
በመ/ፓ/ጠቅላይ ቤተ ክህነት የሰ/ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሓላፊ

የሰ/ት/ቤቶች አንድነት የማኅበራዊ የትስስር ገጾችን ቤተሰብ ይሁኑ!

(የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት)

Youtube

https://www.youtube.com/@eotc-gssu

Facebook

https://www.facebook.com/gssu.eotc

Telegram

https://t.me/eotcgssu21

Tiktok

@eotc_gssu