
ቤተ ክርስቲያን ትውልዱን ለእግዚአብሔር መንግሥት የማዘጋጀት ሰማያዊ ተልእኮዋን በአግባቡ ለመወጣት እና የነገውን ትውልድ ሰብእና በመቅረፅ ረገድ የሰብአዊ ምሕንድስና ሥራዋን ለመፈጸም ዘመኑን የዋጀ አመራርና አሠራር ያስፈልጋታል። ይህም መሻት በብዙ ኦርቶዶክሳውያን ልብ ውስጥ አለ፡፡ ይህ ዕውን ይኾን ዘንድ ዛሬም ኾነ ነገ ቤተ ክርስቲያን ስንዱ እመቤት የሚያሰኛትን የነገረ ሃይማኖት ጥንቃቄ በአስተዳደርና በአመራርም መድገም ስትችል ነው። ቤተ ክርስቲያን በምድር ያለች የእግዚአብሔር መንግሥት ናትና መሠረታዊ መገለጫዎቿ ተጠብቀው ብቻ በምትሰጣቸው የአመራርነት ሚናዋ ተገልጠው ሊታዩ ይገባል። ይህን ዕውን ማድረግም በየዘመኑ የሚነሡ ኖላውያን እና ምእመናን የሁል ጊዜ ሓላፊነት ነው፡፡
በተለይም ቤተ ክርስቲያን ከውጭና ከውስጥ ተገዳዳሪዎች ጋር በተፋጠጠችበት እና እንደ ኢዮብ በፈተና በተከበበችበት በዚህ ዘመን የአሳዳጆቿን በትር መቋቋም የምትችለው በምትሰጠው ውጤታማ አመራር ነው። ፈተናውን ከባድ የሚያደርገው ከውጪው ተጽእኖ በላይ በውስጥ ያለው መንፈሳዊነት መዳከም እና ብልሹ የአስተዳደር ሥርዐት መስፈን ነው፡፡ ስለዚህ ቤተ ክርስቲያን በጥንቱ መንፈሳዊ ልዕልናዋ ጸንታ እንድትቆም ማስቻል እና በዘመኑ የአስተዳደር ጥበብ የተዋጀ አሠራር የሰፈነባት መንፈሳዊ ተቋም ማድረግ በሁለቱ ተገዳዳሪዎቿ የተሴረባትን ሴራዎች ማምከኛ መንትያ መንገዶች ናቸው፡፡
Read more