የአንደኛ ክፍል ፈተና ተሰጠ

በባሕር ዳር ሀገረ ስብከት ሰንበት ት/ቤቶች አንድነት የተሰጠው የአንደኛ ክፍል የአጋማሽ ዓመት ፈተና እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ በተሳካ ሁኔታ መጠናቀቁን የሀገረ ስብከቱ የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት አስታወቀ። ፈተናው እሑድ ፣ ታኅሣሥ 10 ቀን፣ 2014 ዓ/ም የተሰጠ ሲሆን፤ በሀገረ ስብከቱ በሚገኙ እና የአዲሱን ሥርዓተ ትምህርት ትግበራ ባስጀመሩ ሃያ ሰባት ሰንበት ት/ቤቶች የሚገኙ  አንድ ሺህ ሁለት መቶ አርባ ሰባት (1,247) ህጻናት ፈተናውን ወስደዋል።

ከነዚህም ሰንበት ት/ቤቶች መካከል ከፍተኛ ቁጥር ያለው ተማሪ በማስፈተን ቅድሚያውን የወሰዱ ሰንበት ት/ቤቶች የሚከተሉት ናቸው፦

  1. ምሥራቀ ፀሐይ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ሰ/ት/ቤት አንድ መቶ ሃያ አራት (124)  ህጻናት በማስፈተን፣
  2. መንበረ ስብሐት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ሰ/ት/ቤት አንድ መቶ አምስት (105) ህጻናት በማስፈተን፣
  3. የጽርሐ አርያም ደብረ ሲና በዓታ ለማርያም ቤተ ክርስቲያን ሰ/ት/ቤት ስድሳ ዘጠኝ (69) ህጻናትን በማስፈተን፣

ከዚሁ ጋር በማከልም በመጀመሪያው መንፈቀ ዓመት የትምህርት ክፍለ ጊዜ የሚሰጡት የትምህርት ዓይነቶች መሠረተ ሃይማኖት ፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት እና የልሳነ ግእዝ  መሆናቸውን የባሕር ዳር ሀገረ ስብከት ሰንበት ት/ቤቶች አንድነት አስታውቋል።

 

ከቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በዓመት ሁለት ጊዜያት እንዲሆን በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ 5 ቁጥር 164 በተደነገገው መሠረት ምልዓተ ጉባኤው የመክፈቻው ሥርዓተ ጸሎት ከፈጸመበት ከጥቅምት 11 ቀን 2014ዓ.ም. ጀምሮ የተለመደውን ዓመታዊ መደበኛ ስብሰባ ሲያካሂድ ሰንብቶ ለቤተ ክርስቲያናችንና ለሀገራችን የሚበጁ ማህበራዊና መንፈሳዊ ውሳኔዎችን አሳልፎአል፡፡ በዚህም መሠረት፡-

  1. የ2014 ዓ.ም. የጥቅምቱ ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ መክፈቻ መልእክት አሁን በአገራችን እየታየ ባለው ጦርነት እና የርስበርስ ግጭት ላይ ያተኮረ ሲሆን፡-
  • ጦርነቱ በወንድማማቾች መካከል እየተደረገ ያለና ሀዘኑን የከፋ ያደረገው መሆኑ፣
  • በዚሁ ጦርነትና ግጭት በርካታ ኢትዮጵያውያን ወገኖቻችን ለሞት ለስደትና ለረሀብ መዳረጋቸው፣
  • በዚህም ምክንያት በአገሪቱ እየታየ ያለው የኑሮ ውድነት አገራዊ ልማት ላይ እያደረሰ ያለው ተጽእኖ ከፍተኛ መሆኑን በመገንዘብ ይህ ጦርነትና ግጭት ተወግዶ በአገሪቱ ሰላምና አንድነት እንዲሰፍን ከሁሉም በላይ ወደ እግዚአብሔር በመጸለይ ይቅርታ ምሕረት መጠየቅ አስፈላጊ መሆኑን የሚያስገነዝብ በመሆኑ ጉባኤው ይህንኑ መልእክት ተቀብሎ በመላ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ተግባራዊ እንዲሆን ወስኗል፡፡
  1. በአገራችን በኢትዮጵያ አሁን ያለው የሰላም እጦትና ጦርነት ወደፊትም ሊያስከትል የሚችለው ችግር ከፍተኛ መሆኑ ስለታመነበት በተቻለ አቅም ዜጐች ሁሉ ለአገራዊው አንድነትና ሰላም መገኘት ዘብ እንዲቆሙ የየበኩላቸውን ጥረት እንዲያደርጉ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡
  2. በዚሁ አገራዊ የሰላም እጦት እየተደረገ ያለውን ጦርነት ምክንያት አድርገው ከአገር ውጭ የሚገኙ አንዳንድ አብያተ ክርስቲያናትና ካህናት አገራዊ ሰላም ላይ ጥላ በሚያጠላ አገራዊና ሕዝባዊ አንድነትን በሚያፈርስ መልኩ ቅስቀሳ ማድረጋቸው ከቤተ ክርስቲያንና የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች ነን ከሚሉ በፍጹም የማይጠበቅ ሆኖ አግኝቶታል፡፡
    በመሆኑም በአውስትራልያ፣ በካናዳ፣ በአውሮፓና በአሜሪካ ሁነው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስም እየፈጸሙ ካለው አገራዊና ሕዝባዊ አንድነት ከሚያደፈርስ ተግባራቸው እንዲቆጠቡ ቅዱስ ሲኖዶስ እያሳሰበ አሁንም ወደ ሰላሙና አንድነቱ እንዲመለሱ ጥሪውን ያቀርባል፡፡ ይህንንም የሰላም ተልዕኮ የሚያስፈጽም በውጭው ዓለም የሚገኙ ብፁዓን አባቶች የሚመሩት የጋራ የሰላም ልዑክ እንዲቋቋም ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡
  3. በአገራችን በኢትዮጵያ በተከሰተው ጦርነት ምክንያት ከቀዬአቸው ለተፈናቀሉና በተፈጥሮና ሰው ሠራሽ ችግር ለደረሰባቸው ወገኖቻችን ዕርዳታ እንዲሆን ብር 50,000,000.00 (ሃምሳ ሚሊየን ብር) በቤተ ክርስቲያናችን ስም ችግሩ ለደረሰባቸው ወገኖች እንዲሰጥ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡
  4. የአገራችንን ቀጣይ የዕድገት ደረጃ በእጅጉ ከፍ ያደርጋል የሕዝቦችን አኗኗር በመቀየር ከድኀነት ያወጣል በሚል ታስቦበት ከዓመታት በፊት ግንባታው የተጀመረው የሕዳሴ ግድብ እየተጠናቀቀ ያለበት ምዕራፍ ላይ መድረሱና 2ኛ ሙሌት መከናወኑ ለአገራችን ለኢትዮጵያ ትልቅ የድል ምዕራፍ በመሆኑ ቅዱስ ሲኖዶስ አድንቋል፡፡ በቀጣይም ለመጨረሻው የድል ምዕራፍ ለመድረስ መላው ኢትዮጵያውያን በጉልበት በገንዘባቸውም በሐሳብም ጭምር ድጋፋቸውን እንዲያደርጉ ቅዱስ ሲኖዶስ አሳስቧል፡፡
  5. በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሚገኙ መንፈሳውያን ኮሌጆችን አሁን ቤተ ክርስቲያኒቱ ከደረሰችበት የእድገት ደረጃ ጋር ለማመጣጠንና ተጨማሪ ኮሌጆች በማስፈለጉ በደቡብ ክልል የሚገኙ ሁለት ካህናት ማሠልናዎች ወደ መንፈሳዊ ኮሌጅ እንዲያድጉ አስፈላጊውም በጀት እንዲመደብላቸው ጉባኤው ወስኗል፡፡
  6. ለመንበረ ፓትርያርክና ለየአህጉረ ስብከት የሚያገለግል የ2014ዓ.ም. ዓመታዊ በጀት ከመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ተደልድሎ በቀረበው መሠረት ዝርዝሩን ተመልክቶ በጀቱ እንዲፀድቅ በማድረግ በሥራ ላይ እንዲውል ጉባኤው ወስኗል፡፡
  7. የ4ዐኛው አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ የጋራ መግለጫ ላይ የተነጋገረው ጉባኤ በመግለጫው ላይ በመወያየት አንዳንድ ማሻሻያዎችን በማድረግ እና በማጽደቅ የ2014ዓ.ም. በጀት ዓመት የሥራ መመሪያ እንዲሆን ጉባኤው ወስኗል፡፡
  8. በአገራችን በኢትዮጵያ የተደረገው 6ኛ አገራዊ ምርጫ ነጻና ዲሞክራሲያዊ በሆነ መንገድ መከናወኑና በተለይም ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነው በመመረጣቸው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የተሰማውን ደስታ እየገለጸ፤ ቀጣዩ አገራዊ ሥራቸውም ለአገርና ለወገን የሚጠቅም የተሳካ የአመራር ዘመን እንዲሆንላቸው በሥራቸውም እግዚአብሔር አብሮአቸው እንዲሆን ቤተ ክርስቲያን ትፀልያለች፡፡
    በአጠቃላይ ቅዱስ ሲኖዶስ በጉባኤ በሰነበተባቸው ቀናት ስለ አብነት ት/ቤቶች እና ስብከተ ወንጌል መስፋፋት፣ ስለ ሰንበት ት/ቤቶች መጠናከር ስለ አገራዊ ሰላምና አንድነት ሰፊ ምክክርና ውይይት ያደረገ ከመሆኑም በላይ በአገራችን በተከሰተው የሰላም እጦት የደረሰው ጦርነት ረሀብና የጤና ማጣት አብቅቶ ሰላም እንዲሰፍን ቅዱስ ሲኖዶስ ለሰባት ቀናት ጸሎት ያደረገ ሲሆን በቀጣይም መላው ካህናትና ምዕመናን ስለ አገራችን ሰላምና አንድነት እንዲጸልዩ ቅዱስ ሲኖዶስ አጥብቆ አሳስቧል፡፡
    በመጨረሻም ቅዱስ ሲኖዶስ ለ8 ቀናት ሲያከናውን የቆየውን የጥቅምቱ 2014 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ስብሰባ ዛሬ ጥቅምት 18 ቀን 2014 ዓ.ም. በጸሎት ዘግቷል፡፡

እግዚአብሔር አምላክ ለአገራችን ሰላሙን ለመላው ሕዝባችን አንድነቱን ይስጥልን፡፡
ጥቅምት 18 ቀን 2014ዓ.ም.
አዲስ አበባ – ኢትዮጵያ

 

የሰ/ት/ቤቶች ሥርዓተ ትምህርት በሁሉም አጥቢያዎች እንዲተገበር መመሪያ ተላለፈ

በዓለም አቀፍ ሰ/ት/ቤቶች አንድነት ጠቅላላ ጉባኤ በተወሰነው ውሳኔ መሠረት ሁሉም አኅጉረ ስብከት ተዘጋጅቶ የቀረበውን የአንደኛ ክፍል መጻሕፍት ተግባራዊ እንዲያደርጉ ለሁሉም አኅጉረ ስብከቶች ከመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ደብዳቤ ወጣ።

በዚህም መሠረት ሁሉም አኅጉረ ስብከት እስከ አጥቢያ በማሳወቅና ያልደረሳቸው እንዲደርሳቸው በማድረግ በትኩረት እንዲሠራ መመሪያ ተላልፏል፡፡

መጻሕፍቱን ለማግኘት ይህን ሊንክ ይጠቀሙ : ሥርዓተ ትምህርት

ስለ አተገባበር መልእክት ለመላክ የአንድነቱን የቴሌግራም ቻናል ይጠቀሙ

በአዲሱ ሥርዓተ ትምህርት መሠረት የተዘጋጁት የ1ኛ ክፍል መጻሕፍት ተሰራጩ

ሥርዓተ ትምህርቱ በዋናነት በዓለም አቀፍ ደረጃ በሁሉም የኢትዮጰያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አጥቢያ ያሉ ሰንበት ትምህርት ቤቶችን በትምህርት አሰጣጥ ረገድ አንድ የሚያደርገው የሰንበት ትምህርት ቤቶች መማርያ እና ማስተማሪያ ሥርዓተ ትምህርት መጽሐፍ ለአንደኛ ክፍል ተጠናቅቆ ተሰራጨ

የ2014 ዓ.ም መስቀል በዓል የሰ/ት/ቤቶች ዝግጅት ላይ መሆናቸው ተገለጸ

በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በደማቁ ከሚከበሩ የአደባባይ በዓላት መካከል አንዱ የሆነው የመስቀል ደመራ በዓል ዝግጅት ትርኢትና ወረብ ለማቅረብ ከአዲስ አበባ ከሁሉም ሰንበት ትምህርት ቤቶች የተወጣጡ ቁጥራቸው ከ5500 ባላይ የሆነ ወጣቶች ለተከታታይ 25 ቀናት ዝግጅት አደረጉ . . .

በሀገረ ስብከት ደረጃ የሰ/ት/ቤት ተማሪዎቸ ተመረቁ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት በአዲሱ ሥርዓተ ትምህርት መሠረት በሙከራ ትግበራ ላይ የሚገኙ ሰ/ት/ቤቶች አባላት መካከል በከተማ ደረጃ ወጥ ፈተና እንዲወስዱ በማድረግ በሀገረ ስብከት ደረጃ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት በተገኙበት ከ1200 በላይ የሚሆኑ ተማሪዎችንበቀን በ09/01/2014 ዓ.ም በጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽ አስመረቀ።