ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ የክረምት የመምህራን አሰልጣኞች ሥልጠና እየወሰዱ ያሉ መምህራንን ጎበኙ።
(የሰ/ት/ቤቶች አንድነት) ሐምሌ 18/11/2017ዓ.ም
በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምርያ የሰ/ት/ቤቶች አንድነት አዘጋጅነት በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ዩንቨርስቲ እየተሰጠ የሚገኘው የክረምት የመምህራን የአሰልጣኞች ሥልጠና ላይ በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ እና የሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ በመገኘት አባታዊ መልዕክት አስተላልፈዋል።
ብፁዕነታቸው ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለልጁ ለጢሞቴዎስ የተናገረውን “ለወንድሞችህ ይህንን አስተምራቸው” የሚለውን ኃይለ ቃል መነሻ አድርገው አባታዊ መልዕክት ያስተላለፉ ሲሆን ልጄ ሆይ ጆሮህን ለመምህራን ስጥ እንደተባለ ከመምህራን እግር ስር ቁጭ ብለው የሚማሩት ቃለ እግዚአብሔር ለሕይወታች ስንቅ ነውና ቅዱስ ጢሞቴዎስን አብነት አድርጎ በሕይወት መተርጎም ይገባል የተማርነውንም ለወንድሞች ማስረዳት መንገር ይገባል ብለዋል።
በመጨረሻም ሰልጣኞች በተከታታይ በቀንም በማታም እየተሰጣቸው ያለውን ሥልጠና በሚገባ ተከታትለው በየሀገረ ስብከታቸው ሲመለሱ በትኩረት ሊሰሩ ለሌሎችም ሊያጋሩ እንደሚገባ አባታዊ መልዕክት አስተላልፈዋል።
(የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት)