ብፁዕ አቡነ ኤርምያስ የክረምት የመምህራን አሰልጣኞች ሥልጠና እየወሰዱ ያሉ መምህራንን ጎበኙ።
የሰ/ት/ቤቶች አንድነት) ሐምሌ 14/11/2017ዓ.ም
በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምርያ የሰ/ት/ቤቶች አንድነት አዘጋጅነት በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ዩንቨርስቲ እየተሰጠ 7ኛ ቀኑን በያዘው የክረምት የመምህራን የአሰልጣኞች ስልጠና ላይ የሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ኤርምያስ በመገኘት አባታዊ መልዕክት አስተላልፈዋል።
ብፁዕነታቸው ለእናንተ የመንግስተ ሰማያትን ምሥጢር ማወቅ ተሰጥቷችኋል” ማቴ 13፥11 በሚል ርዕስ ቃለ እግዚአብሔርና አባታዊ መልዕክት ያስተላለፉ ሲሆን የመንግስተ ሰማያት ምሥጢር ለማወቅ ጾታና ማዕረግ ሳይለይ ለሁሉም የሰው ዘር የተሰጠ ጸጋ መሆኑንና ይህን ምስጢር አውቆ ማሳወቅ ከመምህራን የሚጠበቅ ተግባር ነው ብለዋል።
አያይዘውም ለሰንበት ትምህርት ቤቶች ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ መሠራት እንዳለበት አሳስበው እንደ ሀገረ ስብከታቸው ሰሜን ወሎ ለሰንበት ትምህርት ቤት አገልግሎት ልዩ ትኩረት በመስጠት ሰልጣኞችን በመላክና በመማርያ መጻሕፍት ግዥ አስፈላጊውን በጀት በመመደብ እየሠሩ መሆናቸውን ተናግረዋል።
በመጨረሻም ሰልጣኞች እየተሰጣቸው ያለውን ሥልጠና በሚገባ ተከታትለው በየሀገረ ስብከታቸው ሲመለሱ በትኩረት ሊሰሩ እንደሚገባ አባታዊ መልዕክት አስተላልፈዋል።
(የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት)