እንደሚታረዱ በጎች ሆንን!

እንደሚታረዱ በጎች ሆንን!

እንደሚታረዱ በጎች ሆንን!

ኢትዮጵያ አገራችን ለረጅም ዘመናት በአኩሪ ባህልና እሴት አሸብርቃ ከእኛ ደረሰች ናት። ለዚህ መልካም እሴት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሚና ጉልህ ነው። ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ግን ወርቅ ላበደረ ጠጠር እንዲሉ ቤተ ክርስቲያን የጥቃት ዒላማ ሆና ብዙ ቀስቶች ሲወረወሩባት ታያል። መንግሥትም አጥፊዎች ላይ ርምጃ ከመውሰድ ይልቅ የጥፋቱ አካልና ተባባሪ በሚመስል መልኩ በገቢርና በዝምታ አጋዥነቱን አሳይቷል። በተለይም የኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት በኦርቶዶክሳውን ላይ እየተፈጸመ ያለውን ጥቃት እንዲያስቆም ሲጠየቅ ጥቃቱን ከመካድ ጀምሮ በግልጽ አጥፊዎችን እስከ መደገፍ የደረሱ ድጋፎችን ሲያደርግ ተስተውሏል፡፡ ቁጣውና ጩኸቱ ጠንከር ሲል ጥቃቱን ለማስቆም ቃል ይገባል፤ ነገር ግን ጩኸቱ በረድ ሲል የተናገረውን ሲፈጽም አይታይም፡፡ እንዲህ መሆኑ ለገዳዮች የልብ ልብ ሰጣቸው፡፡ ቤተ ክህነቱም የክርስቲያኖች ግድያና ስቃይ ደንታ የሚሰጠው አይመስልም። በየቦታው ክርስቲያኖች ሲገደሉ ምንም ካለማለት ደረጃ የደረሰው ምን ነክቶት ነው ያሰኛል፡፡ በአርሲ ዞን የተፈጸመውን ጅምላ ጭፍጨፋ በተመለከተ ኅዳር ፳፬ ቀን ፳፻፲፮ ዓ.ም ያወጣው መግለጫም “የእንጦጦ መምህር ቢናገር በዓመት፣ ያውም እሬትን” የሚያስተርት ነው። የተሰጠው መግለጫ በሟቾቹ ከመቀለድ አይተናነስም፡፡ ችግሩን ለመንግሥትም ሆነ ለዓለም ማኅበረሰብ ለመግለጥ ካስፈለገ በሚገባ አደራጅቶ፣ ብስሉን ከጥሬ ለይቶ፣ እውነት የሆነውን ሐሰት ከሆነው አጣርቶ ነው፡፡ ይህ መግለጫ ግን ድብስብስ ያለ፣ ዓላማው የማይታወቅ ነው፡፡ ቢሆንም ግን በክርስቲያኖች ላይ እየደረሰ ያለው መከራ ማቆሚያ የሌለው፣ ለማስቆም ፍላጎት ያለው የመንግሥት አካልም የሌለ መሆኑን የሚያስገነዝብ መሆኑን መረዳት ይገባል።
በመላ ሀገሪቱ ክርስቲያኖች ተመርጠው መገደል የጀመሩት ኢሕአዴግ ደርግን አስወግዶ ሥልጣን ከያዘ ማግስት ጀምሮ መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ ለውጥ መጣ ከተባለበት ጊዜ ጀምሮ ግን ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡ በተለይም ከሐምሌ ፳፰ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም በጅግጅጋ የተጀመረው ክርስቲያኖችን መርጦ ማጥቃት በመቀጠልም በኦሮሚያ ክልል ምክንያት እየተፈለገ፣ ወፍ በበረረ፣ ዘንግ በተወረወረ ቁጥር ለመከራ ተዳርገዋል፡፡ የዓይናችሁ ቀለም አላማረንም፣ ሃይማኖታችሁን አልወደድነውም እየተባሉ በስቃይ ላይ ቢገኙም ችግሩን የሚፈታላቸው፣ ጩኸታቸውን የሚሰማቸው አልተገኘም፡፡ ይህ ብቻ ሳይሆን በአማራ ክልል ከሚሴ ዞን፣ በ፳፻፲፩ ዓ.ም ሲዳማን ራሷን የቻለች ክልል ለማድረግ መንግሥትን ጠይቀው መልስ የተነፈጋቸው የዞኑ ነውጠኞች ጥያቄውን ውድቅ ያደረጉባቸው ኦርቶዶክሳውያን የሆኑ ይመስል ከየቤታቸው እየተፈለጉ ለሞትና ለመከራ ዳረጓቸው፡፡ ሀብት ንብረታቸው ወደመ፣ ይዞታቸው እየተነጠቀ ለሌላ አካል ተሰጠ፡፡ አብያተ ክርስቲያናት ተቃጠሉ፡፡
ጥቅምት ፳፻፲፪ ዓ.ም ጅዋር መሐመድ ከመንግሥት ጋር በነበረው አለመግባባት ተከበብኩ ባለ ጊዜ ለመከራ የተዳረጉት ክርስቲያኖች ናቸው፡፡ ሰኔ ፳፻፲፪ ዓ.ም የአርቲስት ሀጫሉ ሁንዴሳን መገደል ተከትሎ በክልሉ በሚኖሩ ክርስቲያኖች ላይ መውረድ የጀመረው የመከራ ዝናብ ዛሬ ድረስ አላቋረጠም፡፡ ክርስቲያኖች በክልሉ እንዳይኖሩ በሕግ ባይከለከሉም በአመፅ እና በጉልበት ከተከለከሉ ግን ዓመታት ማለፋቸው የአደባባይ ምሥጢር ከመሆን ደረጃ ላይ ደርሷል፡፡ በተደጋጋሚ ከመንግሥት ጋር ውይይት ተደርጎ ችግሩን እንፈታዋለን እየተባለ ቃል ቢገባም ችግሩ እየባሰበት እንጂ እየተሻለ አለመምጣቱ ቤተ ክርስቲያን የሐዘን መግለጫ ከማውጣት ያለፈ ተግባር መፈጸም እንዳለባት የሚያስገነዝብ ነው፡፡ ግን ይህ ሲሆን አይታይም።
በሰሞኑ በአርሲ ዞን የተፈጸመውን ጥቃት በተመለከተ ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ባወጣው መግለጫ “በሶሌ ዲገሉ እና ጢጆ ለቡ በተባሉ ቀበሌዎች ፳፰ ኦርቶዶክሳዊያን ከየቤታቸው ተለቅመው የተገደሉ ሲሆን ከእነዚህ ውስጥም ፯ቱ ሴቶችና ፳፩ ወንዶች መሆናቸው ታውቋል። በዚህ ጥቃትም እድሜያቸው ከሰባ ዓመት አዛውንት እስከ ሃያ ስምንት ቀን ጨቅላ ሕጻናት ይገኙበታል። በተመሳሳይ በዲገሉ ማርያም ቤተ ክርስቲያን ፭ ኦርቶዶክሳዊያን ከመገደላቸው በተጨማሪ የሦስት ኦርቶዶክሳውያን ቤት ደግሞ ሙሉ በሙሉ ተቃጥሏል። ከዚህ ቀደም በሮቤ አንዲቶ ደብረ ምጥማቅ ማርያም ቤተ ክርስቲያን በዓለ ማርያምን አክብረው ወደ ቤታቸው በመመለስ ላይ የነበሩ ሦስት ኦርቶዶክሳዊያን ጨለማን ተገን ባደረጉ ነፍሰ ገዳዮች መገደላቸው ይታወሳል። የሀገረ ስብከቱ የሥራ ኃላፊዎች ከመንግሥት የጸጥታ አካላት ጋር በተደጋጋሚና ሆን ተብሎ በሚፈጸመው የኦርቶዶክሳዊያን ጥቃት ዙሪያ በጋራ እየሠሩ የሚገኙ ሲሆን በዚህ ዐይነት የጥቃት ተግባር ላይ ተሰማርተው የሚገኙ አንዳንድ አካላት ላይ በመንግሥት በኩል የማያዳግም ርምጃ እንደተወሰደባቸው ሀገረ ስብከቱ በላከው ሪፖርት አረጋግጠዋል” በማለት ዘርዝሮታል።
ቢቢሲ አማርኛ የደረሰውን ጥቃት የዘገበው “በጥቃቱ የቤተሰብ አባላት የተገደሉባቸው በሽርካ ወረዳ፣ የጥዮ ለቡ ቀበሌ ነዋሪ፣ ኅዳር ፲፫ ቀን ፳፻፲፮ ዓ.ም. ግድያው ሲፈጸም በአጋጣሚ በስፍራው ባለመኖራቸው እርሳቸው ቢተርፉም፣ አብዛኞቹ የቤተሰቦቻቸው አባላት እንደተገደሉባቸው ተናግረዋል። በጥቃቱ ባለቤቴ እና ልጄ፣ የአባቴ ልጆች፣ የአባቴ ሚስት፣ እኅቶቼ እና ወንድሞቼ በአጠቃላይ ሰባት ቤተሰብ ተገድለውብኛል። ከቤት ወስደው ነው የጨፈጨፏቸው” ብለዋል በመሪር ሐዘን። ቢቢሲ ባነጋገራቸው ወቅትም ከጥቃቱ የተረፉ የሁለት ዓመት እና የስምንት ዓመት ልጆቻቸውን አሳክመው እየተመለሱ እንደ ሆነ ተስፋ በቆረጠ ሁኔታ ገልጸዋል። በወረዳው ሾሌ ዲገሊቡና ቀበሌ ነዋሪ የሆኑ ሌላ ግለሰብም ባለፈው ሳምንት በተፈጸመው ጥቃት የስምንት ልጆቻው እናት የሆነችው ባለቤታቸው እና የ፲፪ ዓመት ሴት ልጃቸው እንደተገደሉባቸው ለቢቢሲ ተናግረዋል” በማለት ነው።
ከሳምንት በፊት በደራ ወረዳ በክርስቲያኖች ላይ የተፈጸመው ግድያ በልዩ ልዩ ብዙኀን መገናኛ ተዘግቦ አይተናል ሰምተናልም፡፡ እነዚህ ክርስቲያኖች በሰማዕትነት እንዲጠሩ የአምላካችን ፈቃድ ቢሆንም ከክርስቲያኖች የሚጠበቅ ተግባርና ሐላፊነት መኖሩን መዘንጋት አይገባም፡፡ እንዲህ ያለው አሰቃቂ ግድያ ሲፈጸም ጥቃቱን እንዲያስቆም መንግሥትን ከመጠየቅ ጀምሮ ሌሎች ተግባራትን ማከናወንም ይገባል፡፡ ዝም አላችሁ ላለመባል ብቻ ለግብር ይውጣ የሚሰጡ መግለጫዎች ግን ክርስቲያኖችን ተስፋ ያስቆርጣሉ፡፡ ከዚህ በተጨማሪም በአባቶች ላይ ያለው አመኔታ እንዲቀንስ ስለሚያደርግ ሊታሰብበት ይገባል፡፡ መንግሥትም ዜጎቹን ነቅቶና ተግቶ የመጠበቅ ሐላፊነቱን መወጣት ይኖርበታል፡፡

ይህ ዐይነቱ ኦርቶዶክሳውያን ላይ ያነጣጠረ ግድያ እንዲቆምና የወንጀሉ ፈጻሚዎችም ለፍርድ እንዲቀርቡ በሀገረ ስብከቱ በኩል እየተደረገ ያለው ጥረት እንደተጠበቀ ሆኖ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጠቅላይ ጽሕፈት ቤትም በድርጊቱ እጅጉን ማዘኑን እየገለጸ ጉዳዩን ከሚመለከታቸው የመንግሥት አካላት ጋር በመሆን የሚከታተለው መሆኑን ለመግለጽ እንወዳለን። በሌሎች ስፍራዎች የሚያጋጥሙ ተመሳሳይ ጥቃቶችን በእንጭጩ ለመቅጨትና ከሚመለከታቸው የመንግሥት አካላት ጋር በመነጋገር መፍትሔ ማበጀት ይቻል ዘንድ አህጉረ ስብከት ችግሮች በሚያጋጥሙ ወቅት ሪፖርት እንዲልኩ ቀደም ሲል በደብዳቤ በተላከላቸው የስልክና ዘመናዊ የመገናኛ ዘዴዎች አማካኝነት በፍጥነት በማሳወቅ ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ እያሳሰብንና ለሞቱት ኦርቶዶክሳውያን ወገኖቻችን ሁሉ ልዑል እግዚአብሔር መንግሥተ ሰማያትን እንዲያወርስልን በመጸለይ የፌዴራልም ሆነ የክልል መንግሥታት የሚደርሱ ሃይማኖት ተኮር ጥቃቶች እንዲቆሙና መሰል ጥቃት እንዳይፈጸም ለኦርቶዶክሳዊያን ወገኖቻችን ከለላ እንዲሰጡልን እንጠይቃለን̋ ተብሎ የተነገረውን አጠናክሮ መቀጠል እንጂ በቃል እየተናገሩ ከተግባሩ መራቅ ብዙ ዋጋ ያስከፍላል።