እንኳን ለተራዳኢው መልአክ ለቅዱስ ሚካኤል ዓመታዊ መታሰቢያ በሰላም አደረሳችሁ!
#ሚካኤል ማለት መኑ ከመ አምላክ እንደ እግዚአብሔር ያለ ማነው የሚል ትርጉም አለው። ይህም እንደ እግዚአብሔር ያለ በባሕርይው ቅዱስ የሆነ ፣ እንደ እግዚአብሔር ያለ ንጹሐ ባሕርይ ፣ እንደ እግዚአብሔር ያለ ፍጹም ማነው የሚል ነው። ቅድስና ፣ ንጽሕና እና ፍጹምነት የባሕርይ ገንዘቡ የሆነ ከእግዚአብሔር በቀር የለምና። ዘዳ 33፡26

ሰኔ 12 በዚህች ቀን የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል በዓለ ሲመቱ ይታሰባል። እንዲሁም የባህራንን የሞቱን ደብዳቤ ወደ ሕይወት የቀየረበት እንዲሁም ቅድስት አፎምያን ከሰይጣን ያዳነበት መታሰቢያ ነው። “በመንገድ ይጠብቅህ ዘንድ ወዳዘጋጀሁትም ስፍራ ያገባህ ዘንድ፥ እነሆ፥ እኔ መልአክን በፊትህ እሰድዳለሁ።” ዘጸ 23፡20 ይህ መልአክ በብሉይ እስራኤል ዘሥጋን ከግብጽ ባርነት መርቶ ነጻ እንዳወጣቸውና ምድረ ርስት ከንዐንን እንዲወርሱ በመንገዳቸው ሁሉ እንደረዳቸው፤ እንደጠበቃቸው ሁሉ ባሕራንም ይሄድ ከነበረበት የሞት መንገድ ሕይወትን ሰጥቶ ፤ አፎምያን ደግሞ ከጥንተ ጠላታችን ከዲያብሎስ እጅ በተራዳኢነቱ አድኖ ለክብር አብቅቷቸዋል።

በባሕራን እና በቅድስት አፎሚያ ታሪክ ውስጥ የምናገኘው የመልአኩ ተራዳኢነት ዛሬ ላይ ላለነው ለክርስቲያኖች በሕይወታችን ውስጥ የመልአኩን ተራዳኢነት አምነን እንድንጠቀም ትልቅ ትምህርት የሚሰጥ ነው። ቅዱስ ሚካኤል ወይም ቅዱሳን መላእክት በሰዎች የዕለት ተዕለት ሕይወት ውስጥ መዳን መንግሥተ ሰማይን ለመውረስ በሚደረጉ ሒደቶች ሁሉ የሚራዱና የሚያግዙ ናቸው። ቅዱስ ጳውሎስ በዕብራውያን መልእክቱ ላይ “ሁሉ መዳንን ይወርሱ ዘንድ ስላላቸው ለማገዝ የሚላኩ የሚያገለግሉም መናፍስ አይደሉምን?” ብሏል። ዕብ 1፡14 ዛሬም እኛ ከቅዱሳን መናፍስት ወገን አንዱና አለቃቸው የሆነ ቅዱስ ሚካኤል መዳን መንግሥተ ሰማይን እንወርስ ዘንድ የሚላክ የሚያገለግል አይደለምን እንላለን። ማመን መጠመቅ በጎ ሥራ መሥራት ሕጉን ትዕዛዙን መጠበቅ ንስሐ መግባት እነዚህ በሙሉ ወደ መዳን / መንግሥተ ሰማያት / የሚያደርሱን መንገዶች ናቸው ፡፡
የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል

ለሰዎች የሚራራ ፣ በተጨነቁም ጊዜ የሚያረጋጋ ፣ በደከሙ ጊዜ የሚያበረታ ፣ ባዘኑ ጊዜ የሚያጽናና ነው። ሉቃ 22፡43 ፣ ዳን 10፡20

የሰው ልጆችን ከመከራ ሥጋ እና ከመከራ ነፍስ የሚያድን የሚታደግ ነው። መዝ 33፡7 ፣ ዘፍ 48፡16 ፣ ዕብ 1፡14

ሰውን ከሚገጥመው ክፉ ነገር ሁሉ ይራዳል። ዳን 10፡13 ፣ ዳን 12፡1

ስለ ሰዎች ይማልዳል ከአምላካቸው ያስታርቃል። ዘካ 1፡12-13

ለሰው ሁሉ በጎን የሚያደርግ መልአክ ነው። ሔኖክ 6፡1-2

የከበረ መልአክ ነው። ከክብሩ የተነሳም ምድር ሁሉ ትበራለች። ራእ 10፡1 ፣ ራእ 18፡1

ትሕትናን የሚያስተምር ትሑት መምህረ ትሕትና ነው። ይሁ 1፡9

በሰዎች ድኅነት ሀሴት ደስታን የሚያደርግ ነው። ሉቃ 15፡7
የመልአኩ የቅዱስ ሚካኤል ተራዳኢነቱ አማላጅነቱ በዚህም ዓለም በወዲያኛውም ዓለም ይጠብቀን።