የ2017 ዓ.ም የክረምት የአሰልጣኞች መምህራን ሥልጠና ተጀመረ

ሰ/ት/ቤቶች አንድነት) ሐምሌ 07 2017 ዓ.ም

የ2017 ዓ.ም የክረምት የአሰልጣኝ መምህራን ሥልጠና በዛሬው ዕለት በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ዩኒቨርሲቲ ተጀመረ። በዛሬው የመክፈቻ መርሐ ግብር ላይም አረጋዊው አባት ብፁዕ አቡነ ዘካርያስ ምዕራብ ጎጃም ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እንዲሁም መጋቤ ሐዲስ ጸጋ ወልደ ትንሣኤ የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሐላፊ የተገኙ ሲሆን ብፁዕነታቸው “እነሆ ጊዜው ደረሰ” በሚል መነሻ ቃለ ወንጌል ፣ አባታዊ ምክርና ቃለ ምዕዳን ለሰልጣኝ መምህራኑ አስተላልፈዋል። “እርሱም በውኃ ፈሳሾች ዳር እንደ ተተከለች፥ ፍሬዋን በየጊዜዋ እንደምትሰጥ፥ ቅጠልዋም እንደማይረግፍ ዛፍ ይሆናል፤” የሚለውን የልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊትን ቃል መነሻ በማድረግ የማደራጃ መምሪያው ሐላፊ የእንኳን ደህና መጣችሁ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል። በዛሬው የመክፈቻው መርሐ ግብር ላይ ሰልጣኞች በሚኖራቸው ቆይታ ሊያውቋቸው የሚገቡ ጉዳዮችን በሚመለከት ገለጻ ተሰጥቶ የመክፈቻ መርሐ ግብሩ ፍጻሜ ሆኗል። ሥልጠናው በዛሬው ዕለት በምሽት የሰንበት ት/ቤቶች መዋቅራዊ አደረጃጀትን በሚመለከት የሚቀጥል ሲሆን እስከ ሐምሌ 20 ድረስ በተከታታይ ለ15 ቀናት የሚቆይ ሲሆን የቅድስት ቤተ ክርስቲያን መሠረተ እምነትን ፣ የተለያዩ ክህሎትን የሚያዳብሩ እንዲሁም በሥርዓተ ትምህርቱ ላይ ትኩረት ያደረጉ ከ15 በላይ ሥልጠናዎችን የሚያገኙ ይሆናል። ሥልጠናውን ከ30 ሀገረ ስብከት የተወጣጡ 213 መምህራን የሚወስዱ ይሆናል።

(የሰ/ት/ቤቶች አንድነት)