የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሐላፊ መጋቤ ሐዲስ ጸጋ ወልደ ትንሣኤ በ14ኛው ዓለም አቀፍ የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ላይ ያስተላለፉት መልእክት
የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሐላፊ መጋቤ ሐዲስ ጸጋ ወልደ ትንሣኤ በ14ኛው ዓለም አቀፍ የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ላይ ያስተላለፉት መልእክት
“ወይረድአነ ለነ ድካመነ በመንፈስ ቅዱስ – ድካማችንን በመንፈስ ቅዱስ ያግዛል፡፡ ሮሜ 8፡26
ከሁሉ በማስቀደም አምላካች ቅዱስ እግዚአብሔር እንደ ሐዋርያት በተስፋ ለምንጠብቀውና ኃይል መንፈሳዊም አግኝተን ለበለጠ ሥራ ለምንነሳበት ለበዓለ ጰራቅሊጦስ፣ ለሰንበት ትምህርት ቤቶች ቀን እና ለ14ኛው ዓለም ዐቀፍ የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ጠቅላላ ጉባኤ በሰላምና በጤና አደረሰን አደረሳችሁ፡፡ እንኳን ደህና መጣችሁ።
መንፈስ ቅዱስ የደከሙትን የሚያበረታ ያዘኑትን የሚያጽናና የታወኩትን የሚያረጋጋ ኃጢአተኞችን የሚያነጻ መንፈስ ነውና በደከምን ጊዜ ብርታትን፣ በመከራ ጊዜ ጽናትን፣ በፍርሐት ጊዜ ጥብአትን፣ በሁከት ጊዜ መረጋጋትን ይሰጠናል፡፡
በዘመነ ሐዋርያት የነበረው አገልግሎት በሰይፍና በስለት ውስጥ አልፎ የጠፉትን መፈለግ፣ በሞት ተወራርዶ በጎችን፣ ጠቦቶችንና ግልገሎችን መጠበቅን የሚጠይቅ ነበርና የሚያደክሙና የሚያፍገመግሙ ውስጣዊና ውጫዊ ፈተናዎች በርካቶች ቢሆኑም ሲፍገመገሙ ያጸናቸው በድካማቸውም ሁሉ ያገዛቸው የብርታታቸውና የጽናታቸው ምክንያት መንፈስ ቅዱስ ነውና “ወይረድአነ ለነ ድካመነ በመንፈስ ቅዱስ-ድካማችንን በመንፈስ ቅዱስ ያግዛል” በማለት ሐዋርያው ተናገረ፡፡
ይህ ታላቅ የቤተ ክርስቲያን የልደት ቀን የሆነው በዓለ ጰራቅሊጦስ በ፭ኛው ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ዘመነ ፕትርክና በቅዱስ ሲኖዶስ መልካም ፈቃድ የሰንበት ትምህርት ቤቶች ቀን ተብሎ ከተሰየመ እነሆ ዛሬ ፲፬ኛ ዓመት ላይ እንገኛለን፡፡ ባለፉት 14 ዓመታት መንፈስ ቅዱስ ድካማችንን እያገዘ ብዙ መልካም ሥራዎችን ለማከናወን በመቻላችን የጅማሬም የፍጻሜም ባለቤት የሆነውን ልዑል እግዚአብሔርን እናመሰግናለን፡፡
ዕለተ ጰራቅሊጦስ ሐዋርያት በአንድ ሐሳብ በአንዲትም ልብ ሆነው በተሰበሰቡባት ጽርሐ ጽዮን መንፈስ ቅዱስ ወርዶ ሁሉም የራሱን ቋንቋ በሚሰማበት ልሳን እንዲያስተምሩ የተለያዩ ልሳኖች ለሐዋርያት የተገለጡባት፣ ፍርሐት ጠፍቶላቸው ጥብአትን ገንዘብ ያደረጉባት ዕለት ናት።
ይህችን ዕለት መነሻ በማድረግ በየዓመቱ በበዓለ ጰራቅሊጦስ ዕለት የሰንበት ትምህርት ቤቶች ቀን የሚያከብረው የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያም እንደ ሐዋርያት አንድ ልብ በመሆን ከመምሪያው የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት ጋር የሊቃውንት ጉባኤ አባላትን፣ የመንፈሳዊ ዩንቨርስቲና የኮሌጆች መምህራንን እንዲሁም የሥርዓተ ትምህርት ባለሙያዎችን በማሳተፍ በተዘጋጀው ወጥ የሰንበት ትምህርት ቤቶች ሥርዓተ ትምህርት መሠረት ሁሉም እንደ እድሜው ደረጃ ሊረዳው በሚችለው ልክና አቅም በተለያዩ ልሳናት መጻሕፍትን በማዘጋጀት ስያሜውን በተግባር በማሳየት ላይ ይገኛል።
ይህም ውጤት ከዚህ ቀደምም በተግባር የታየና ዛሬም በአማርኛና በአፋን ኦሮሞ ታትመው ለምረቃ በተዘጋጁት መጻሕፍት የተረጋገጠ እውነት ነው፡፡ ወደ ፊትም በመንፈስ ቅዱስ እርዳታ በተለያዩ የሀገር ውስጥና የውጭ ሀገር ቋንቋዎች መጻሕፍቱን ለማሳተም በዝግጅት ላይ ነን፡፡
ይህ ሁሉ ዘመን ተሸጋሪ የሆነና በዘላቂነት ትውልድን የሚታደግ ሥራ የተሠራውና እየተሠራም ያለው “ወሀሎ ምስሌሆሙ ኅቡረ መንፈስ ቅዱስ” መንፈስ ቅዱስ በጉባኤያቸው ሁሉ አብሯቸው ነበር እንዲል መጽሐፈ ምስጢር በሥራችን ሁሉ መንፈስ ቅዱስ ስላልተለየን በድካማችንም ስላገዘን ነው።
ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስ ከወረደላቸው በኋላ በሁሉም ቋንቋ ባስተማሩት ትምህርት ብዙ ነፍሳትን ማርከው “ምንተ ንግበር አኃዊነ” እንዳሰኙ ሁሉ በእነዚህ ፲፬ ዓመታት በተለይም ባለፉት ሁለት እና ሦስት ዓመታት በትኩረት በተሠራው ሥራ እና በመንፈስ ቅዱስ የሚመራው ቅዱስ ሲኖዶስ ለሰንበት ት/ቤት አገልግሎት በሰጠው ትኩረትና በፈቀደው በጀት በ2016 ዓ.ም ከ1ኛ እስከ 4ኛ ክፍል በአማርኛ፣ በዚህ ዓመት በ2017 ዓ.ም ከ5ኛ እስከ 7ኛ ክፍል በአማርኛ እና ከ1ኛ እስከ 4ኛ በአፋን ኦሮሞ የሰንበት ት/ቤት መማሪያ መጻሕፍት በመታተማቸው ያለቋንቋ ገደብ ወጣቶችንና ሕጻናትን በማስተማር ግልገሎችንና ጠቦቶችን የመጠበቅ የመምሪያውን ተልእኮ ለማስፈጸም ትልቅ በር ተከፍቷል፡፡ በሥርዓተ ትምህርቱም ቤተ ክርስቲያናቸውን በሚገባ ያወቁና የተረዱ፣ በሥነ ምግባርም አርዓያ፣ “ምንተ ንግበር” በማለትም የቤተ ክርስቲያን ተስፋ የሚሆኑ ወጣቶችን ለማፍራት የተሻለ ዕድል ተገኝቷል፡፡
ወደፊትም በቤተ ክርስቲያናችን በ10 ዓመቱ መሪ ዕቅድና በዚህ ጠቅላላ ጉባኤ በጸደቀው የ5ዓመት ሥልታዊ ዕቅድ እየተመራን የበለጠ ለመሥራት የምንጥር መሆናችንን እየገለጽኩ እና የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽሕፈት ቤት ልዩ ክትትልና የቅዱስነትዎ አባታዊ መመሪያ፣ ጸሎትና ቡራኬ እንዳይለየን በታላቅ ትሕትና እየጠየቅሁ በመንፈስ ቅዱስ አጋዥነት የማደራጃ መምሪያው ሠራተኞችና የመምሪያውን ተልዕኮ ለማስፈጸም በቅዱስ ሲኖዶስ ፈቃድ ከተዋቀረው የመምሪያው የሀገር አቀፍ ሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ሥራ አመራርና ሥራ አስፈጻሚ እንዲሁም ልዩ ልዩ አገልጋዮች ጋር በመሆን፣ በመምሪያው ሊቀ ጳጳስ መመሪያ ሰጪነት ታግዘን ከምንጊዜው በተሻለ ውጤታማ ሥራ በመሥራት ላይ እንገኛለን፡፡
በአጠቃላይ በዘንድሮው የጉባኤያችን መሪ ቃል “የመንፈስንም ሰይፍ ያዙ እርሱም የእግዚአብሔር ቃል ነው፡፡” ብሎ ሐዋርያው እንደተናገረው የሰንበት ት/ቤት ወጣቶችና ሕጻናት መንፈሳዊ ሰይፍ የሆነውን ቃለ እግዚአብሔርን በአግባቡ ታጥቀው ክህደት ጥርጥርና ኑፋቄን ቆርጠው ይጥሉበት ዘንድ በ2017 ዓ.ም ዕቅዳችን ከፍተኛ ትኩረት ሰጥተነው የነበረው የሰንበት ት/ቤት መማሪያ መጻሕፍትን ቀጣይ ኅትመት የማከናወን ተግባር ተሳክቶ በዕቅዳችን መሠረት ከ5ኛ እስከ 7ኛ ክፍል በአማርኛ ከ1ኛ እስከ 4ኛ ክፍል በአፋን ኦሮሞ ማሳተም በመቻላችን እግዚአብሔርን እናመሰግናለን፡፡
በሚቀጥለው በ2018 በጀት ዓመት እግዚአብሔር ቢፈቅድ ቀሪዎቹ ከ8ኛ እስከ 12ኛ ክፍል ያሉ መጻሕፍት የአርትዖት ሥራን በልዩ ትኩረት በማጠናቀቅ ለማሳተምና በተመሳሳይ በአፋን ኦሮሞም ቀጣይ የትርጉም፣ አርትዖትና የኅትመት ሥራን ለመሥራት ከወዲሁ ዝግጅት ጀምረናል፡፡
በመጨረሻም በ10 ዓመቱ የቤተ ክርስቲያናችን መሪ ዕቅድ መሠረት የተዘጋጀውን የ5 ዓመቱ ስልታዊ ዕቅድ አግባቡ በለመተግበር እንችል ዘንድ በእነዚህ ሁለት ቀናት በሚኖረን የምክክር መድረክ በዓለ ጰራቅሊጦስንና ዓመታዊ የሰንበት ት/ቤቶችን ቀን እያከበርን በቀጣይ ሥራዎቻችን ዙሪያ በትኩረት ተመካክረን የሚጠብቀንን ሰፊ አገልግሎት ባገናዘበ መልኩ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን የሚጠቅም፣ የወጣቱንም ሕይወት የሚታደግ ምክክር እንድናደርግ በትሕትና አሳስባለሁ፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
መጋቤ ሐዲስ ጸጋ ወ/ትንሣኤ
የሰ/ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሐላፊ
ግንቦት 30 ቀን 2017 ዓ.ም
(የሰ/ት/ቤቶች አንድነት)
የሰ/ት/ቤቶች አንድነት የማኅበራዊ የትስስር ገጾችን ቤተሰብ ይሁኑ!
Youtube
https://www.youtube.com/@eotc-gssu
Facebook
https://www.facebook.com/gssu.eotc
Telegram
https://t.me/eotcgssu21
Tiktok
@eotc_gssu