ብፁዕ አቡነ ቀለሜንጦስ የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ እና የሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በ14ኛው የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ጠቅላላ ጉባኤ ያስተላለፉት መልእክት

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ፩ዱ አምላክ አሜን።

“ሀበነ ንኅበር በዘዚአከ መንፈስ ቅዱስ-በአንተ ሕልውና ባለ መንፈስ ቄዱስ አንድ እንሆን ዘንድ አንድ መሆንን ስጠን” (ቅዳሴ ሐዋርያት ምዕ ፪ ክፍል ፪፥፴፬)

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣

ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ የምስራቅ ትግራይ ራያ ሀገረ ስብከትና የማሕበራት ማደራጃ መምሪያ ሊቀ ጳጳስ፣

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር አሀጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣

የመ/ፓ/ጠ/ቤ/ክ የመምሪያና የድርጅት ሓላፊዎች፤

እንዲሁም ሰንበት ትምህርት ቤቶቻችሁን ወክላችሁ ከየ ሀገረ ስብከቱ የመጣችሁ የሰንበት ት/ቤ/ቶች ክፍል ሓላፊዎችና የአንድነት አመራሮች

በዚህ ጠቅላላ ጉባኤ ላይ የተገኛችሁ ውሉደ ቤተ ክርስቲያን በሙሉ፤

“አቀድም አእኵቶቶ ለእግዚአብሔር በእንተ ኵልክሙ እስመ ተሰምዐት ሃይማኖትክሙ ውስተ ኵሉ ዓለም”። መሰብሰባችን፣ ጽንዐ ሃይማኖታችን በዓለም ሁሉ ተሰምቶዋልና  በዚህ ጉባኤ ላይ እንድንገኝ እንድናመሰግነውም የፈቀደልንን ልዑል እግዚአብሔርን ከሁሉ በማስቀደም እናመሰግናለን።

እንኳን ለ፲፬ኛው ዓለም አቀፍ የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት ጠቅላላ ጉባኤና በዓለ ጰራቅሊጦስ አደረሳችሁ!! እንኳንም ደህና መጣችሁ ለማለት እወዳለሁ።  በመቀጠልም፦ቅዱሳን ሐዋርያት “ሀበነ ንኅበር በዘዚአከ መንፈስ ቅዱስ በማለት የአንድነታቸው ማኀተም በሆነው መንፈስ ቅዱስ ኀብረታቸው እንዲጸና ለምነዋል የዚህም ታላቅ ጉባኤ ዓላማ ሕብረተ መንፈስ ቅዱስን አጽንቶ ትውልድን በቀናች ሃይማኖት ለማነጽ በመንፈስ ቅዱስ እርዳታ የተሰጠንን ኃላፊነት ለመወጣት ነው። እንደሚታወቀው ሕብረት ማለት የእርስ በርስ ግንኙነት ማለት ሲሆን ሕብረት ማድረግ ያስፈለገው አንድ ሰው ብቻውን ምንም ማድረግ ስለማይችል ነው። ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን አገልግሎቷ ሁሉን አሳታፊ ነው። ቅ.ዳዊት “ናሁ ሠናይ ወናሁ አዳም ሶበ ይሄልዉ አኃው ሕቡረ” ወንድሞች በኅብረት ቢኖሩ መልካም ነው በማለት ኅብረት መልካምና የተወደደ መሆኑን ገልጦልናል። ሕብረታችንን ደግሞ የሚያጸናው ፍቅር ነው ያለ ፍቅር ሕብረት ትርጉም የለውም በሕብረት ውስጥ የፍቅርን የበላይነት ቅዱስ ጳውሎስ ሲያስረዳን በልሳን ብናገር ትንቢትንም ሁሉ ባውቅ ሥጋዬንም ለእሳት አሳልፌ ብሰጥ ፍቅር ግን ከሌለኝ ከንቱ ነኝ በማለት ግልጹን ነግሮናል።1ኛቆሮ ፲፫፥፪ ቅዱሳን ሐዋርያትም መንፈስ ቅዱስ የወረደላቸው አብረው ስለተሰበሰቡ ብቻ አይደለም በአንድ ልብ በአንድ ሀሳብ በፍቅር ጸንተው ስለጠበቁት ነው።(ግሐ ፪፥፵፪) የተከበራችሁ የዚህ ታላቅ ጉባኤ ተሳታፊዎች እንዲሁም በመላው ዓለም ያላችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን፦ ይህን የሚያክል ታላቅ ሕብረት ፈጥረን በመካከላችን መለያየት ካለ ትርፉ ድካም ብቻ ነው እግዚአብሔርም በመካከላችን አይገኝም። መለያየት ዲያብሎስ ቤተ ክርስቲያንን ለማጥቃት ከሚጠቀምበት  መሣሪያ አንዱ ስለሆነ፤ሀበነ ንሕበር በዘዚአከ መንፈስ ቅዱስ እያልን በመማጸን ሕብረታችንን እናጽና።

ቅዱስ አባታችን ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣

ክቡራን የዚህ ታላቅ ጉባኤ እድምተኞች ይህ በየ ዓመቱ በእለተ ጰራቅሊጦስ እየተከናወነ ያለው ጠቅላላ ጉባኤ ዘርፈ ብዙ መንፈሳዊ ፍሬ ያፈራ ጉባኤ ነው፤ ባሳለፍናቸው 3 ዓመታት እንኳን ለረዠም ዓመታት የተደከሙባቸው ሥርዓተ ትምህርት ትግበራ እና የመማሪያ መጻሕፍት ሕትመት ተግባራዊ ሆኖ ፍሬውን ለማየት በቅተናል፦ በሀገር ውስጥና በውጭው ዓለም የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት ተጠናክሮ ዘመኑ በፈቀደልን ቴክኖሎጂ በመጠቀም ተናቦ ለመስራትም ተችሎዋል። ይህም የሆነው የቅዱስ ሲኖዶስ የቅርብ ክትትል ስላልተለየን የቅዱስ አባታችን ጸሎት እረድቶን የመንፈስ ቅዱስ እገዛ ተጨምሮበት ነው። በተጨማሪም፦ ያላቸውን ጥሪው ሸጠው በአንድነት ለመኖር ወስነው የመንፈስ ቅዱስ እርዳታ እንደጎበኛቸው  መቶ ሃያው ቤተሰብ በሀገር አቀፍ ደረጃና በውጭው ዓለም እያገለገሉ ያሉ ልጆቻችን ያላቸውን እውቀት፣ጉልበት፣ገንዘብና ጊዜአቸውን ያለ ምንም ስስት  በማዋጣት እያበረከቱ ያለው የአንድ ልብ አገልግሎትም ውጤት ነው። ለዚህም መንፈሱን ልኮ ዘወትር ከሕብረታችን ያልተለየው እግዚአብሔርን ሳመሰግን በታላቅ ደስታ ነው። ወደ ፊትም ከዚህ የበለጠ ሰፊ ሥራ የሚጠብቀን መሆኑን ለአፍታ እንኳን የምንዘነጋው አይደለም ጀመርን እንጂ አልጨረስንምና።

ቅዱስ አባታችን ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣

ትውልዱ በጥያቄና በብዙ ፍላጎት የተሞላ ስለሆነ ዘመኑም ውስብስብና አስጨናቂ በመሆኑ በትውልዱ ላይ የተጫነው ዓለም አቀፍ ጫና ያለ እግዚአብሔር ቃል የሚታለፍ ስላልሆነ ከሥራችን ጎን ለጎን ብርቱ ጸሎትና ያላሰለሰ ክትትል ከምን ጊዜውም በላይ ያስፈልገናልና በጸሎታችሁ ይህን ጉባኤ እንድታስቡት እማጸናለሁ። በመጨረሻም የቤተ ክርስቲያኒቱን ጥሪ አክብራችሁ የትውልዱ ባለ አደራነታችሁን ተረድታችሁ በዚህ ታላቅ ጉባኤ ላይ ከሩቅም ከቅርብም የተገኛችሁ የቤተ ክርስቲያናችን ልጆች እናንተንም የወከላችሁንም ሀገረ ስብከት በታላቅ አክብሮት እናመሰግናለን። በምትቆዩባቸው ጊዜያት ሁሉ ዓለም እንደ ሚያገሳ አንበሳ ዙሪያውን በተለያዩ ርኩሰቶች አድብታ ለምትጠብቃቸው የዚህ ዘመን ትውልድ የሚጠቅም ፍሬአማ ውይይት እንድታደርጉ እያሳሰብኩ መልእክቴን አጠቃልላለሁ።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር!!!